13

.

"በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው::" የማቴዎስ ወንጌል 7: 4

"እናንተ የተጠማችሁ ሁሉ፥ ወደ ውኃ ኑ፥ ገንዘብም የሌላችሁኑና ግዙ ብሉም ኑ ያለ ገንዘብም ያለ ዋጋም የወይን ጠጅናወተት ግዙ።" ትንቢተ ኢሳይያስ 55 : 1

Friday, October 14, 2011

6ቱ ቃላተ ወንጌል

በዲ/ን ቴዎድሮስ ጌታቸው
የቦ/መ/ብ/ቅ/እግዚአብሔር አብ ቤ/ክ ም/ስብከተ ወንጌል ኃላፊ

ወደ ሴት አትመልከት በልብህም አታመንዝር፡፡ ማቴ. 5፤28
ይህ ወደ ሴት በመመልከት በልቡና የሚያድረው ፍትወተ ሥጋ ኃጢአት መሆኑን የሚያመለክት ነው፡፡ ሴትን ማየት ሳይሆን ባዩአት ጊዜ ለፈቃደ ሥጋ መመኘትን ነው፤ እግዚአብሔር የማይፈቅደው ለዚህም ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  በወንጌል “ወደ ሴት ያየ ሁሉ የተመኛትም ያን ጊዜ በልቡ ከእርሷ ጋር አመንዝሯል፡፡” በማለት የተናገረው፤ “አይቶ የማይሰናከል ዓይን” የተባለውን ፍትወተ ተራክቦን አውጥቶ መጣልና መንግሥተ ሰማያትን ገንዘብ ማድረግ በማየት የሚመጣ ምኞትን በመፈጸም በገሃነም ከመጣል እጅጉን ይሻላል፤ ይበልጣልም፡፡ ማቴ. 5፤28
አንዳንድ ጊዜ  ሰዎች የሚያነሱት ጥያቄ አለ፤ ጥያቄውም በእምነት ውስጥ  ያሉትንም የሚጨምር ነው፤ ይኸውም ዓይን የተፈጠረው ለማየት ነው፤ ስለዚህ ማየት እንዴት ኃጢአት ሊሆን ይችላል ይላሉ፡፡ ነገር ግን ሊስተዋል የሚገባው አንድ ነገር አለ፤ ጌታችንም በወንጌል ሲያስተምር ወደሴት ያየ ብቻ አላለም፤ ይህ ማለት ማየት ብቻውን ኃጢአት አይደለም ማለት ነው፡፡ ነገር ግን የተመኛት ቢኖር “ያን ጊዜ በልቡ አመነዘረ” ነው ያለው፡፡ ይህ ማለት አንድ ወንድ አንዲ ሴትን ተመልክቶ በልቡ ከርሷ ጋር በዝሙት ለመውደቅ መመኘቱ ነው ትልቁ ኃጢአት ምክንያቱም ያ ሰው በልቡ ያለውን የዝሙት ስሜት ለመፈጸም የተመቻቸ ሁኔታ ስለሌለ እንጂ በልቡ ያንን ክፉ ኃጢአት ፈጽሞታልና ነው፡፡ በቅዱ መጽሐፍም ላይ ምኞት የሚያመጣውን ኃጢአትና በደል እንማራለን፡፡ አዳምና ሔዋን ዕፀበለስ የማይጠቅማቸው እደሆነ በአምላካቸው ቢነገራቸውም እነርሱ ግን ለመብላት ጎመጁ፤ ተመኙ፤ ነው የሚለን፤ ነገር ግን ይ ክፉ ምኞታቸው የሞትን ሞትን አመጣባቸው፡፡ ዘፍ. 3፤1-24
ታላቁ አባታችን ቅዱ ዳዊት በእግዚአብሔር እንደ ልቤ የተባለው አባት በሕይወቱ ዘመን እግዚአብሔርን የበደለበትና ያሳዘነበትን ኃጢአት የፈፀመው ከክፉ የሥጋ ምኞት የተነሳ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ 2 ሳሙ.11፤1-26 ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብም እግዚአብሔር ማንንም በክፉ እንደማይፈትን ነገር ግን ሰው በሥጋዊ ምኞት ሲጓዝና ሲታለል እንደሚፈተን አስተምሯል፡፡ ያዕ. 1፤12-15
ስለዚህ ዓይን ሁሉን ይመለከታል ወደ ልቡና መዝገብ የሚልከው ግን ቀልቡ ያረፈበትን ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ወንድ ሴትን፤ ሴትም ወንድን በክፉ የኃጢአት ምኞት መመልከት አይገባም፤ በልቡናም ለዝሙትና ለሥጋ ፈቃድ ማሰብ ታላቅ በደል ነው፡፡ የሀሳብ ፍጻሜው ተግባር ነው፤ የሥጋ ምኞት ኃጢአትን ይወልዳል፡፡ የኃጢአት ክፍያው ደግሞ ሞት ነው፡፡ ያዕ. 1፤15 ስለዚህም በማየት (በመመኘት) መዘዝ ከሚመጣ ውድቀት ለመዳን ይህን ሕገ ወንጌል በሚገባ መረዳትና ዓይነ ሥጋን ብቻ ሳይሆን ዓይነ ልቡናንም መቆጣጠር ያስፈልጋል፡፡ በተለይ በወጣትነት ዘመን ላለን ሁሉ ትልቁ ፆር ይህ ዓይነቱ ነውና ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው ከክፉ የጎልማሳነት ምኞት በመሸሽ ሰውነታችንን ለቅድስናና እግዚአብሔርን ደስ ለሚያሰኝበት ሕይወት እንድናዘጋጅ ቸሩ አምላካችን ይርዳን፡፡
ይቆየን

ጥምቀት

ትምህርተ ሃይማኖት
በመምህር ፍቅረማርያም ባዘዘው
የቦሌ መ/ብ/ቅ/እግዚአብሔር አብ ቤ/ክ የመጽሐፍ መምህር
ጥምቀት
ጥምቀት ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ከዘጠኙ አበይት በዓላት መካከል ሲሆን፤ ይህ የጥምቀት ስርዓት የሚካሄደው በመዝፈቅ ነው፡፡ ይህም፤
V  ጥምቀት ዳግመኛ ተወልደን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የምንገባበት ምሥጢር ነው፡፡ ዮሐ.3፤5
V  በጥምቀት ኃጢአት ይሰረያል ሐዋ. 2፤8
V  መንጻትና መቀደስም በጥምቀት ነው፡፡ 1ኛ ጴጥ. 3፤21
የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀት
ይህ ጥምቀት የሰው ልጆች የዕዳ ደብዳቤ የተደመሰሰበት ጥምቀት ነው፡፡ ይህ ማለት ሰይጣን በአዳምና በሔዋን አገዛዝ አጽንቶባቸው በነበረ ሰዓት እኛ የአንተ ባርያ ነን በማለት “አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ፤ ሔዋን አመቱ ለዲያብሎስ” የሚል የዕዳ ደብዳቤ አንዱ በዮርዳኖስ አንደኛው ደግሞ በሲዖል ጥሎት ነበር፤ በዮርዳኖስ ያለው በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀት ተደምሷል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል “ወደምሰሰ ለነ መጽሐፈ ዕዳነ በሥርያቱ እምዕደውነ” ቆላስይስ 2፤14 ይህም ማለት የዕዳ ደብዳቤያችንን ከባላንጋራችን ከዲያብሎስ አጠፋልን (ደመሰሰልን) ማለት ነው፡፡ ይህ  የዕዳ ደብዳቤ የባርነት ደብዳቤ ነበር፡፡ ጌታችን በዮርዳኖስ ሲጠመቅ እንደሰውነቱ ረግጦ፤ እንደአምላክነቱ አቅልጦ አጥፍቶልናል፡፡ ቅዱስ ኤፍሬምም “ወሰጠጠ መጽሐፈ ዕዳዎሙ ለአዳም ወለሔዋን፤ የአዳምንና የሔዋንን የዕዳ ደብዳቤ ደመሰሰላቸው”” ነው የሚለው የሰኞ ውዳሴ ማርያም፡፡ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀት ለእርሱ የሚጠቅመው ሆኖ ሳይሆን መጠመቁ ለእኛ ክብር ነው፡፡
ትንቢተ ሕዝቅኤል 36፤25 “ጥሩ ውሀንም እረጫችኋለሁ እናንተም ትጠራላችሁ፤ ከርኩሰታችሁም ሁሉ ከጣዖቶቻችሁም ሁሉ አጠራችኋለሁ፡፡” አለ፤ ይህም የሚያስተምረን በጥምቀት የነጻን የተቀደስን እኛ መሆናችንን ነው፡፡ የጌታችን ጥምቀትን ስናስብ የተቀደስንበትና የነጻንበት የዕዳ ደብዳቤያችን የተደመሰሰበት መሆኑን ነው፡፡
ጥምቀቱን በውሀ ያደረገበት ምክንያት
ውሀ ድሀ፤ ባለፀጋ ሳይል በሁሉም የሚገኝ በመሆኑ እንዲሁም ውሀ ብንጠጣው ሕይወት የሚሆን፤ ታጥበን የምንነጻበት …ወዘተ በመሆኑ ጌታም የመጣ ለሁሉም ሰው እንዲሁም ድሀ ባለጸጋ ሳይል ሁሉንም የሚያፈቅር አባት መሆኑን ለማስተማር ነው፡፡
ጥምቀቱን በዮርዳኖስ ስለምን አደረገው
1.  ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው የአዳምና የሔዋን የዕዳ ደብዳቤ አንዱ በዮርዳኖስ ስለነበር ያን ለመደምሰስ ነው፡፡
2.  ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ እንደሚጠመቅ ትንቢት ተነግሮ ነበር፡፡                                          መዝ. 113፤3-6
3.  በዮርዳኖስ ንህማን ከለምጹ የተፈወሰበት ነው፡፡ 2ኛ. ነገ.5፤8- ፍጻሜ
4.  አባታችን ኢዮብ የተፈወሰበት ነው፡፡
ጌታችን በ30 ዓመቱ ለምን ተጠመቀ
ብዙ ጊዜ ሰዎች የሚከራከሩበት በመሆኑ ነው፤ ይህም አንዳንዶቹ “ጌታ የተጠመቀ በ30 ዓመቱ ነውና እኛም እንደ እርሱ በ30 ዓመት መጠመቅ አለብን” ይላሉ፡፡ ይህ ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ  ጋር እኩል ነኝ እንደማለት ነውና አቅምን ማወቅ ጥሩ ነው፡፡ አዳምና ሔዋንም የወደቁት እንደ አምላካቸው እንሆናለን ብለው ነበር፡፡ “ጌታችን ለምን በሰላሳ ዓመቱ ተጠመቀ” ተብሎ ይጠየቃል እንጂ “እኔም እንደእርሱ በሰላሳ ዓመት መጠመቅ አለብኝ” ሊሆን አይችልም፤ ይህንን የምትሉ ወንድሞችና እህቶች ካላችሁ ስህተት ነውና ተመለሱ እንላለን፡፡ ጥቂት ቆይታችሁ ደግሞ እንደጌታ እንሰቀላለን እንደምትሉ ፍርሃቱ አለን፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰላሳ ዓመቱ መጠመቁ ምሥጢሩ ግን እንዲህ ነው፤ አዳም ሲፈጠር የ30 ዓመት ጎልማሳ ሆኖ ነበር፤ ይህ የ30 ዓመት ጎልማሳ አዳም ልጅነቱን አስወግዶ፤ ክብሩንም አጣ፡፡ ስለዚህ የአዳም ልጅነት የሚመለስለት ጌታችን በ30 ዓመቱ ሲጠመቅ በመሆኑ ነው፡፡ ክርስቶስን “ሁለተኛ አዳም” ያልነውም የመጀመሪያው አዳም ያጣውን በረከት በሁለተኛው አዳም በኢየሱስ ክርስቶስ ሕይወትን በማግኘቱ ነው፡፤ ስለአዳም ልጅነት ነው በ30 ዓመቱ የተጠመቀ እንጂ እናንተም በሰላሳ ዓመታችሁ ተጠመቁ እያለን አልነበረም፡፡
የእኛ ጥምቀት በ40 እና በ80 ቀን መሆኑ
1.  ሔዋን በተፈጠረች በ80 ቀን፤ አዳም ከተፈጠረ በ40 ቀን ነበር ገነት የገቡት፡፡ ይህም በተወለድን ወንዶች በ40 ቀን፤ ሴቶች በ80 ቀን ወደ ቤተመቅደስ መግባት እንዳለብን ነው የሚያስተምረን፡፡ (መ.ኩፋሌ 4፤9-11፤ መ.ዘሌዋውያን 12፤1-5፤ ሉቃ. 2፤21-24)
2.  ሕፃናት በብሉይ ኪዳን ሲገረዙ ክብርን ያገኙ ነበር፤ ፀጋውን ለይቷቸው አያውቅም፡፡ (ዘፍ.17፤11) ለምሳሌ
·         ነቢዩ ኤርምያስ የተቀደሰው በእናቱ ማኅጸን ነበር፡፡ (ት.ኤር. 1፤5)፤
·         መጥምቁ ዮሐንስ በእናቱ ማኅጸን በመንፈስቅዱስ ተመልቶ ነበር፡፡ (ሉቃ. 1፤15)
·         ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚያስተምርበትም ሰዓት ሕፃናትን ባርኳቸዋል፤ ይህም ሕፃናት በዕድሜያቸው ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ የሚከለክላቸው አለመሆኑን ያሳያል፡፡ (ማቴ. 19፤13-15፤ ማር. 1፤13-15)
·         ቅዱስ ጳውሎስ በ1ኛ ቆሮንቶስ 1፤16 ላይ የእስጢፋኖስን ቤተሰቦች በሙሉ እንዳጠመቀ ይናገራል፡፡ ቤተሰብ ሲል ደግሞ ከሕፃን እስከ ሽማግሌ ድረስ ያለው መሆኑ አያጠያይቅም፡፡ ስለዚህ “ሰላሳ ዓመት ሲሞላኝ ነው መጠመቅ ያለብኝ” የሚል ሰው ከመጽሐፍቅዱስ ጋር ገና ግንኙነት ያላደረገ ወይንም መጽሐፍቅዱስ ምን እንደሚል ያልተገነዘበ ሰው ነው፡፡
በማን ስም እንጠመቃለን
“በስመ ሥላሴ” በማቴዎስ ወንጌል ም.28፤19-20 “ወደ ዓለም ሂዱ ፍጥረትን ሁሉ አስተምሩ በአብ በወልድ በመንፈስቅዱስ ስም አጥምቋቸው” ይላል፡፡ አንድ አንድ ሰዎች በሐዋርያት ሥራ በምዕራፍ 2 ላይ ያለውን በመያዝ “ሐዋርያት ያጠምቁ የነበር በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ነው እንጂ በሥላሴ ስም አይደለም፤ ስለዚህ እኛም መጠመቅ ያለብን በኢየሱስ ስም ነው” ይላሉ፡፡ ይህ ግን ስህተት ነው፤ ምክንያቱም ኢየሱስ ክርስቶስ አጥምቁ ብሎ የላካቸው በአብ በወልድ በመንፈስቅዱስ ስም ነው፡፡ እነርሱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እያጠመቁ አብ እና መንፈስቅዱስን ዘንግተዋቸው አይደለም፡፡ ነገር ግን፤
1.  የዮሐንስ ወንጌል ም.14፤8 “እኔን ያየ አብን አይቷል፤…. እኔ በአብ እንዳለሁ አብም በእኔ እንዳለ አታምንምን” ብሎ ተናግሮ ነበር፡፡ እነርሱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ሲያጠምቁ አንድነታቸውንና ሦስትነታቸውን ጠንቅቀው ስለአወቁ እንጂ ጠፍቷቸው አይደለም፡፡
2.  የኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር አብ ልጅ እንደሆነ ራሱ ቅዱስ ጴጥሮስ መስክሮ ነበር፡፡ (ማቴ. 16፤17)
ስለዚህ በወቅቱ አወዛጋቢ እና መፍትሔ ጠፍቶለት የነበር ችግር የእግዚአብሔር ሰው የመሆኑ ምሥጢር ነበር፡፡ ታዲያ ሐዋርያት በሥራቸው ሁሉ ስለኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት እንዲሁም አዳኝነት መመስከር ስለነበረባቸው ብዙ ጊዜ የኢየሱስ ክርስቶስን ስም ይጠሩ ነበር፤ ዛሬ ሁሉ አማኝ ነው፤ በማን ስም መጠመቅ እንዳለበት ያውቃል፡፡ ስለኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት ያልገባው ሰው ብቻ ነው ስለእርሱ አምላክነት አስተምረህ የምታጠምቀው፡፡
የነገረ መለኮት ሊቃውንት “There is no baptism without Holy Spirit” ይላሉ ይህም ማለት በጥምቀት አብ ወልድ መንፈስቅዱስ ከሌሉበት፤ የእነርሱ ስም ካልተጠራ ያ ጥምቀት “ጥምቀት” አይባልም በውሀ ተነክሮ እንደመውጣት ያህል ነው ይላል፡፡ በዮርዳኖስ አብ በደመና “የምወደው ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት” ሲል መንፈስቅዱስ በአምሳለ ርግብ ሲወርድ መታየቱ ሰው በሥላሴ ስም መጠመቅ እንዳለበት የተገለፀ ምሥጢር ነው፡፡ ለዚህ ነው የነገረ መለኮት ሊቃውንት “In the river Jordan is revealed the mysteries of Holy Trinity – that mean without Holy Trinity no baptism.” (The scholars of Theology) ያሉት፡፡
በኦሪት ዘፍጥረት ምዕ. 1፤2 “የእግዚአብሔር መንፈስ በውሀ ላይ ሰፍፎ ነበር” ይላል፡፡ ይህ ማለት ውሀን የሚያጠራ ለሰው ሁሉ ተስማሚ እንዲሆን የሚያደርግ መንፈስቅዱስ መሆኑን የሚገልጽ ሲሆን በተጨማሪ ግን ምሥጢራዊ ትርጉም ነው፡፡ ቅዱስ ጄሮም እንዲህ ሲል ይገልጸዋል፤
“The symbol of Baptism. It is mystical meaning “the Spirit was stirring above the waters” already at that time baptism was being flourish ad owed. It caused not,  be true baptism, to be sure, without the Spirit.” (St. Jerom) “በውሀ ላይ ሰፍፎ የነበረው መንፈስ የጥምቀት ምሳሌ ነው፡፡ ይህም ምሥጢራዊ ትርጉም ያለው ነው፤ ያለ መንፈስቅዱስ ጥምቀታችን እውነት አይሆንም” ነው የሚለው፡፡
የትርጓሜ መጻሕፍት መምህራንም የጥምቀት ምሳሌ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ “ውሀ በልብ የሚሳቡትን፤ በእግር የሚሽከረከሩትን ፤ በክንፍ የሚበሩትን አስገኝቶ ነበር፡፡ ይህም ማንኛውም ሰው በጥምቀት የሚወለደው ልደት ነው፤ ከሥጋ የተወለደው የሰው ልጅ በመንፈስ ሲወለድ ረቂቅ ምሥጢር ይገለጽለታል” ይላሉ፡፡ “በብዙ አቅጣጫ መንቀሳቀስ ይችላል፤ ሰማያዊ ፀጋ እንዲሁም ምድራዊ ፀጋ ይበዛለታል” ይላሉ፡፡ ስለዚህ ጥር 11 ቀንን ስናስብ ብሔራዊ ባህላችን ነው፤ ዓለም ሁሉ በጉጉት የሚጠብቀው በዓል ነው፡፡ በየዓመቱ ስናከብረው ሁልጊዜ በየዓመቱ እያጠመቅን አይደለም፤ አንዳንዶች “ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ በየዓመቱ ታጠምቃለች” ይላሉ፤ ጥምቀት አንዲት መሆኗን የምትመሰክር ሃይማኖት መሆኗን ሁሉም ያውቀዋል፡፡ (ኤፌ. 4፤4) ይህ ግን ክርስቶስ ለእኛ ሲል መጠመቁን ከገሊላ ወደ ይሁዳ (ዮርዳኖስ) ሄዶ መጠመቁን ለማመልከት አባቶቻችን ታቦታትን ከክብር መንበሩ ወደ ጥምቀተ ባሕር ይዘው በመሄድ የጌታን ትህትና እያስተማሩ እንጂ ሁልጊዜ ማጥመቃቸው አይደለም፡፡
ስለጥምቀት ያላችሁን ጥያቄ በሙሉ ለዝግጅት ክፍሉ በመላክ ለጥያቄዎቻችሁ ተገቢውን ሰፋ ባለ መልኩ ለመመለስ እንደሚቻል ለማሳወቅ እንወዳለን፡፤
የሰላም በዓል ያድርግልን፡፡


ምንጭ፡ የቦ/መ/ብ/ቅ/እግዚአብሔር አብ ቤ/ክ ሰ/ት/ቤት ፍኖተ ብርሃም መጽሔት ጥር 13/ 2003 ዓ.ም

ቅኔ

 በመሪጌታ አዲስ መሀሪ
የቦ/መ/ብ/ቅ/እግዚአብሔር አብ ቤ/ የቅኔ መምህር
የ “ቅኔ” ማለት ምን ማለት ነው
ቅኔ የሚለው ኃይለ ቃል መገኛው “ቀነየ” ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ገዛ ማለት ነው፡፡ በግስ ርባታ “ወ”ን እና “የ”ን መድረሻ ያደረገ ማንኛውም የግስ ዓይነት ደጊመ ቃል ካልኖረው በስተቀር ጎርዶ ወይም ሳይጎርድ ይነገራል፡፡ ለምሳሌ፡ “ቅኔ” የሚለው ቃል የተገኘው ቀነየ ከሚለው የግስ መድረሻ ፊደል “የ”ን ጎርዶ የተነገረ መሆኑን ከቃሉ ላይ መረዳት ይቻላል፡፡ “ቅኔ” የሚለው ቃል በተለያዩ የመስኩ ሊቃውንት ፤ መምህራን የተለያየ ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ “ቅኔ”ን አንዳንዶች “ሰርዋድ” ሲሉት አንዳንዶች ደግሞ ጥሬ ዘር ይሉታል፤ ይህም የአረባብ ዘዴውን በተመለከተ ሲሆን የቃሉ ትርጉም ደግሞ ግዛት፤ አገዛዝ የሚል አንድምታ ይኖረዋል፡፡
የቅኔ ባህርይ
ቅኔ በውስጡ ብዙ ነገሮችን ይይዛል፤ በተለያዩ የግዕዝ ቃላት፤ የአነባበብ ክምችት፤ የተለያየ ሙያ ባላቸው አገባቦችና ቃላት የሚገነባና የሚዋብ መሠረቱ የጸና የሃይማኖት ግንብ ነው፡፡ አገባብ ማለት በመስተዳምርነት የሚያገለግሉ የግእዝ ቃላትን የያዘ ማለት ነው፡፡ በአማርኛ ትምህርታችን በመስተምርነት የሚያገለግሉ ቃላትን እንደሚከተለው እንመለከታለን፤ እንደ፤ እንዲ፤ እንዳ፤ እንድ  እና ሆኖም፤ ስለሆነ፤ ይልቁንም፤ ነገር ግን የመሳሰሉት ናቸው፡፡ እኚህ የአማርኛ መስተዳምር ቃላት የተወለዱት ከዚሁ ከጥንታዊው ቋንቋችን ማህፀን ነው፡፡ እራሱ የሀገሪቱ የሥራ ቋንቋ ሆኖ እያገለገለ ያለው “አማርኛ” ሳይቀር የተወለደው ከግእዝ መሆኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን በዓለም ደረጃ የታወቀ ነው፡፡ አማርኛ ከግእዝ የተወለደ ለመሆኑ ማስረጃ አያስፈልገንም ምክንያቱም አሁን በዘመናችን ከግእዙ እየተነጠቁ ወደ አማርኛው ቋንቋ እየተዳቀሉ ያሉ የግእዝ ቃላትን መመልከቱ ብቻ በቂ ይሆናል፡፡ ለምሳሌ፡ “ሙስና” የሚለውን ቃል ስንመለከት በሀገሪቱ ውስጥ ባሉ ታላላቅ ሰዎች ሲነገርና ሲወራ እየሰማን ነው፡፡ ቃሉ “ማሰነ” ከሚለው የግእዝ ቃል የተወሰደ ነው፤ ትርጉሙም ጠፋ ማለት ሲሆን ጉበኝነትን ለማውገዝ የተጠቀሙበት ቃል ነው፡፡ የቃሉ ትክክለኛ ትርጉም “ጥፋት” የሚል ሆኖ ጥፋት የሚለው ቃል ሲተነተን በእሳት የመጥፋት እና በመቅሰፍት የመጥፋትን ሁኔታ የሚያሳይ እንደሆነ ሊቃውንት ይተነትናሉ፡፡ በሌላ በኩል “መስተዳምር” የሚለው ቃል የአማርኛ አያያዥ ቃላትን ወክሎ የምናገኘው ቃል ሲሆን የቃሉ ዋና መገኛው ደግሞ “አስተዳመረ” ከሚለው ግስ ሆኖ ትርጉሙም አያያዘ አንድ አደረገ ማለት ነው፡፡
ቅኔ፡ ሰፊና ለምርምር ፈጠን የሚያደርግ፤ ለግኝትና ለድርሰት ብቁ የሚሆን ዘርፈ ብዙ ጥቅም ያለው ነው፡፡ የቅኔ መዋቅራዊ ይዘት ከእብራይስጥ፤ ከግሪክና ከዐረብኛ ቋንቋዎች ጋር ከፍተኛ ዝምድና እና ትስስር አለው፡፡ ለዚህም ከግእዝ ቋንቋ ውስጥ ወስደን በንጽጽር መልክ እናያለን፡፡ “ርሑቅ” ይላል የቃሉ ትርጉም “እሩቅ” ማለት ሲሆን በእብራይስጥ ደግሞ “ርሖቅ” ሲል ይደመጣል ትርጉሙም ከግእዙ ጋር ተመሳሳይ ስለሆነ “እሩቅ” የሚል ሆኖ እናገኘዋልን፡፡ ግእዝ በአጠቃላይ ከእብራይስጥ፤ ከግሪክ እና ከዐረብኛ ቋንቋዎች ከፊደል መመሳሰል ጀምሮ እስከ ቋንቋው መዋቅራዊ ሥርዓት ድረስ እጅግ በጣም የተቀራረበ ስልት እና ትርጉም ይታይበታል፡፡ ቅኔ ማህበራዊ ጠቀሜታው የላቀ ነው፤ የረዘመውንና የተንዛዛውን አሳጥሮ የሚፈለገውን መልእክት ለማስተላለፍ ይጠቅማል፡፡
በአንድ ማኅበረ ሰብእ ውስጥ ቋንቋ ከፍተኛ ሚና ይጫወታል፡፡ ከተለያዩ ሰዎች ጋር የባህር ልውውጥ ለማድረግና ለመገበያየት በሰፊው ያገለግላል፡፡ ለምሳሌ፡ እንግሊዘኛን ብንወስድ የዓለማችን መገናኛ እና መግባቢያ በመሆኑ ብዙሃን የሚሆነው የዓለማችን ሕዝብ በመጠኑም ቢሆን ይናገረዋል፡፡ በዓለማችን ላይ የሚሰሩት ሞባይልን ጨምሮ የተለያዩ ማሽኖች በብዛት የሚሰሩት የዚህን ቋንቋ ተናጋሪ ህዝብ ታሳቢ በማድረግና ማዕከል በማድረግ ነው፡፡ ይህ ሲባል ሌላ ቋንቋ አያስፈልግም ለማለት አይደለም፡፡ በዓለማችን ላይ በሺህ የሚቆጠሩ ቋንቋዎች አሉ፡፡ ኢትዮጵያን ብንወስድ ከ80 በላይ ቋንቋዎች አሏት፡፡ እኚህም ቋንቋዎች ብርቅዬና የማይጠገቡ ልዩ ስጦታዎቻችን ናቸው፡፡ በሀገሪቱ ውስጥ ከሚገኙት ቋንቋዎች ውስጥ የግእዝ ጥንታዊ ብሄራዊና ታሪካዊ ቋንቋ በመሆኑ እንዴት ማሳደግና በብዙሃኑ ዘንድ እንደቀድሞው አገልግሎቱን ይስጥ ጥያቄያችን ሊሆን ይገባል ይህ ቋንቋ የ80 ሚሊየን የኢትዮጵያ ህዝብ ሀብት ነውና፡፡ ቅኔ የሚለው ብሂልም የተገኘው የኢትዮጵያ የመጀመሪያ ቋንቋ ከሆነው የግእዝ ቋንቋ ነው፡፡ በሀገሪቱ ውስጥ ታሪካውያን ቦታዎች የግእዝን ማንነት ከፍ አድርገው ይናገራሉ፡፡ የቱሪስት መስህብ በመሆን የዓለምን ሕዝብ ቀልብ በቁጥጥር ስር ያደረጉ ከድንጋይ ተፈልፍለው የታነጹ አብያተክርስቲያናት እና ሐውልቶች በሙሉ መግባቢያቸው የግእዝ ቋንቋ መሆኑን ይናገራሉ፡፡
የዘመናችን ወጣት ሆይ በፍልፍል ዋሻዎችና ገዳማት ውስጥ ለጥበብና ለምርምር ሊሆኑ የሚችሉ እና ድብቅ የጥበብ ምንጭነት ያላቸው የብራና መጻሕፍት  የሚዳስሳቸው አጥተው ወርቃቸውንና ጠገራ ብራቸውን የቀበሩበትን ቦታ ሳይጠቁሙን በሞት ዋዜማ ላይ ይገኛሉና ንቃ ብለን የውርስ ባለቤት መሆን ይኖርብናል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ወራሽ የሌላቸው ተብለው ባዕድ ለመውረስ ቅድመ ዝግጅቱን እያጠናቀቀ መሆኑን መግለጥ እንሻለን፡፡ ለምሳሌ፡ የተለያዩ ጠቃሚነታቸው የላቀ አያሌ በብራና የተጻፉ የምርምር መጻሕፍት እንደ በእንግሊዝና ጀርመን የመሳሰሉት ሀገራት እየተወሰዱ ለእነርሱ አዲስ ግኝት እና ምርምር ፍንጭ ሆነዋቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሥርዓተ አምልኮውን  የሚፈጽመው በግእዝ ቋንቋ መሆኑን ለጸሎት የምንጠቀምባቸው መጻሕፍት ዋቢ ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ለምሳሌ፡ መዝሙረ ዳዊት፤ ድጓ፤ ጾመ ድጓ፤ መጽሐፈ ቅዳሴ፤ ጸዋትውና ምዕራፍ የተሰኙት ጥቂቶቹ የሥርዓተ አምልኮቱ መፈጸሚያ መጸሕፍት ናቸው፡፡
በመሆኑም በቤተክርስቲያናችን አጠቃላይ ቁልፍ ሚና የሚጫወተው የ”ቅኔ” ትምህርት ነው፡፡ ስለሆነም ያለዘርና ሃይማኖት ልዩነት ከእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የሚጠበቅ ቢኖር ቅኔን ከነ ግእዝ ቋንቋ ጠንቅቆ ሊያጠኑት እና ሊመሩበት ይገባል እንላለን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር


ምንጭ፡ ፍኖተ - ብርሃን መጽሔት በቦ/መ/ብ/ቅ/እግዚብሔር አብ ቤ/ክ ሰ/ት/ቤት የታሕሳስ/2003 ዓ.ም እትም



የትምህርተ ሃይማኖት መቅድም

በመምህር ፍቅረማርያም ባዘዘው
የቦ/መ/ብ/ቅ/እግዚአብሔር አብ ቤ/ክ የመጽሐፍ መምህር
የትምህርተ ሃይማኖት መቅድም
በባለፈው ጽሑፋችን “ከእውቀት በፊት እምነት” እንደሚቀድም በጥቂቱ መሰረታዊውን መልእክት ለማስተላለፍ የተሞከረበት ነበር፡፡ ታዲያ ይህ ሃይማኖት ከእውቀት በፊት ዝም ብለን የምንቀበለው ለምንድን ነው የሚል ጥያቄ በእያንዳንዳችን አዕምሮ ውስጥ ያቃጭልብን ይሆናል ለዚህም እንደሚከተለው እንገልጻለን፡፡
í. እምነት ከአእምሮ (ከእውቀት) በላይ ነው፡፡
ምንም ያህል አዋቂዎች ብንሆን ከአእምሮ በላይ የሆነውን እግዚአብሔርን ልናውቀው አንችልም፡፡ አእምሮ ገደብ አለው፤ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው “ድንግል ሆይ የልጅሽን እራሱን በራሱ የሚሰውርበትን የባሕርይውን ጥልቀት፤ ምልዐት፤ ርቀት ሊመረምር ይወዳል ነገር ግን አልመረመረው ብሎ እንደ ባሕር ማዕበል ወዲያና ወዲህ ያማታዋል” ይላል፡፡ ይህ የሚገልጸው የሰውን ልጅ የእውቀት ገደብ ነው፡፡ እውቀታችን የተገደበ ነው፤ “ሰው እንዲህ ባለ አእምሮ እንዲያስብ እንጂ ማሰብ ከሚገባው አልፎ በትዕቢት እንዳያስብ ከመካከላችሁ ላለው ለእያንዳንዱ እመሰክራለሁ፡፡” ይላል፡፡ ሮሜ. 12፤3 ስለዚህ የሰው ልጅ የማይችለውን ነገር ሊያደርግ ቢፈልግ አይችልምና መቀበል ይኖርበታል ማለት ነው፡፡ በዚህ ዓለም ውስጥ ያለ ዕውቀት ደግሞ ምንም አይደለም፡፡ 1ኛ ቆሮ. 1፤20 “ጸሐፊ ማን ነው ጠቢብስ ማን ነው እግዚአብሔር የዚህን ዓለም ጥበብ ከንቱ (ስንፍና) አድርጎታል” ይላልና፡፡
î. እምነት ከስሜት በላይ ነው፡፡
ይህ ሲባል ስሜት ከሕዋሳት የምናረጋግጠው ነው፤ እግዚአብሔር ረቂቅ አምላክ (መንፈስ) ነው፤ ሥራዎቹ በአጠቃላይ መንፈሳዊ ናቸው እንጂ ቁስ አካል አይደሉም፡፡ ይህን መንፈሳዊ ሥራ በስሜት እንረዳዋለን እንኳን ብንል ከድካም ውጭ ሌላ  ፋይዳ አይኖረውም፡፡ ስለዚህም በስሜት የምንረዳው ሳይሆን የምንቀበለው ነው፡፡ ዮሐ.4፤24 “እስመ እግዚአብሔር መንፈስ ውእቱ፤ እግዚአብሔር መንፈስ ነውና፡፡” 1ኛ ቆሮ.3፤16
ï. ሃይማኖት በተስፋ የሚረዱት ነው፡፡
“ሃይማኖትሰ ጥይቅት ይእቲ ለዘይሴፍዋ፤ ሃይማኖት ተስፋ ለሚያደርጓት የተረዳች ናት” ዕብ. 11፤1 ስለዚህም ተስፋ የሌለው ሰው አያምንም፤ ካላመነ ደግሞ ተስፋ የለውም ማለት ነው፡፡ ሁልጊዜ በየደቂቃው የምንደግመውን ጸሎት ማለትም “አቡነ ዘበሰማያት” የሚለውን ጸሎት ብንመለከት “መንግሥትህ ትምጣ” ስንለው ዓይን ያላያትና ጆሮ ያልሰማትን መንግሥተ ሰማያትን ነው፡፡ ይህን የሚያደርገው ደግሞ ከማመን ጋር ተስፋ ሲኖረው ነው፡፡ ሃይማኖት የሌለው ሰው ግን ተስፋ አይኖረውም፡፡ ስለዚህ ይህን ዘለዓለማዊ መንግሥት ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያወርሰንን የምናረጋግጠው በሃይማኖት ብቻ ነው፡፡
የእግዚአብሔርን ቸርነት ረድኤትና ጸጋ እንዲሁም ጥበቃውን አምነን የምንጠብቀው በተስፋ ነው፡፡ ትውክልቱን በእግዚአብሔር ላይ ያደረገ ሰው ሁልጊዜ በተስፋ ይጠብቀዋል፡፡ እርሱ እግዚአብሔርም ይህንን ተስፋ (ተምኔት) ለሚጠባበቁት ሰዎች በእርግጥም የሚዘገይ አይደለም፡፡ ምን አልባት እንኳን ቢያዘገየው ሳያስብልን ርቶ ሳይሆን የለመነው ነገር ለእኛ ስለማይሆነን ብቻ ነው፤ ሰው እግዚአብሔርን ሲጠይቅ እኔ ያልኩት ይሁን ሳይሆን “አንተ ያልከው ይሁን” ብሎ መለመን አለበት፡፡ ቅዳሴ “ያረምም ከመ ዘኢይሰሚ ይጎነዲ ከመዘ ኢይሁል፤ እንደማይሰማ ዝም ይላል እንደማይሰጥ ይዘገያል” ይላል፡፡ ይሰጣል ነገር ግን ይዘገያል የሰዎቹ እምነት የሚረጋገጠው፤ ስለሰጠን ብቻ የምናምንበት ከሆነ እምነት አይደለም፡፡ እምነት ግን በእሳት ውስጥ ተፈትነው የሚያልፉበት የሕይወት መንገድ ነው፤ የነፍስ እረፍትም ይገኝበታል፡፡ ት.ኤር.6፤16 “በመንገድ ዳር ቁሙ የትኛው መንገድ መልካም እንደሆነ መርምሩ በዚያም ሂዱ በነፍሳችሁ እረፍትን ታገኛላችሁ” ይላልና፡፡ በእውነትና በሃይማኖት (በተስፋ) ለሚለምኑት ሰዎች ግን የዘገየ ቢመስል አይዘገይም፤ እርሱም አያስቀረውምና፡፡ በሕይወተ ሥጋ እያሉ ይቅርና ሙሴ በሕይወት ዘመኑ የተመኘውን ነገር ሳያይ ቢሚትም ጌታችን ግን ሙሴን ከመቃብር ውስጥ አስነስቶ በሕይወቱ ዘመን የጠየቀውን ጥያቄ እሙን ሲያደርግለት ይስተዋላል፡፡ (ዘጸ.33፤17፤ ማቴ.17፤3)
እግዚአብሔርን በተስፋ (በእምነት) ለሚጠባበቁት ሁሉ ከችግር የመቃብር ኑሮ ውስጥ ነገ እንደሚነሱ የተስፋ ትንሣኤ እንዳላቸው ሁሉም ሊያምነው ግድ ይላል፡፡
ይቆየን!

Thursday, October 13, 2011

ትምህርተ ጦም በሊቃውንት



 በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

 
አንድ የገዳም አበምኔት  አንድ ወቅት አባ ጳይመን የሚባሉትን አባት “እግዚአብሔርን መፍራት እንዴት ገንዘቤ ማድረግ ይቻለኛል” ብለው  ይጠይቋቸዋል፡፡ እሳቸውም ሲመልሱ “እንዴት ሰው በላመና በጣፈጠ መብልና መጠጥ ሆዱን እየሞላ እግዚአብሔርን መፍራት ገንዘቡ ሊያደርግ ይችላል? ስለዚህም ጦም እግዚአብሔርን ወደመፍራት ይመራል፡፡ የጦም የመጨረሻ ግቡ እግዚአብሔርን ወደመፍራት ማምጣት  ነው”  ብለው ይመልሱላቸዋል፡፡
 
አንድ ወቅት አንድ ጠዋሚ በጦም ወቅት ማልዶ ይርበዋል፡፡ እናም ከሦስት ሰዓት በፊት ላለመመገብ ከፍላጎቱ ጋር ይሟገታል፡፡ ሦስት ሰዓትም ሲሆን እንደምንም ብሎ እስከ ስድስት ሰዓት ሊቆይ ይወስናል፡፡ ስድስት ሰዓት ደርሶ ሊመገብ ማዕዱን በቆረሰ ጊዜ እንደገና ለራሱ እስከ ዘጠኝ ሰዓት ልቆይ ብሎ በመናገር ምግቡን ከመመገብ ይከለከላል፡፡ ዘጠኝ ሰዓት ላይ ጸሎቱን አድርሶ ሊመገብ ሲል ሰይጣን ልክ እንደጭስ ከሰውነቱ ሲወጣ ታየው ወዲያው ረሃቡ ጠፋ፡፡
 
እየጦምክ ነውን? ለተራበ አብላ ፣ለተጠማም አጠጣ፣ ሕመምተኞችን ጎብኝ፣ የታሰሩትን ጠይቅ፣ በመከራ ላሉት እራራላቸው፣ በጭንቀት ወድቀው የሚያለቅሱትን አጽናናቸው፣ ርኅሩኅ፣ ትሑት፣የዋህ፣ ሰላማዊ፣ አዛኝ፣ይቅር ባይ፣ እውነተኛ እና ታማኝ ሁን፡፡ እንዲህ ከሆንክ እግዚአብሔር ጦምህን ይቀበልልሃል፡፡ ስለንስሐም ብዙ የንስሐ ፍሬን ይሰጥሃል፡፡ ጦም ለነፍስ ምግብ ነው፡፡
 ቁጣ መቼም ቢሆን የሚመከር አይደለም፤በተለይ በጦም ሰዓት ከቁጣ መራቅ ተገቢ ነው፡፡ ትሕትናንና ፣የዋሃትን ገንዘብህ አድርግ፤ክፉ ፈቃዶችንና አሳቦችን ተቃወማቸው፤ ራስህን መርምር በየእለቱ ወይም በሳምንት ውስጥ ምን መልካም እንደሠራህ አእምሮህን ጠይቀው፡፡ እንዲሁም ምን ስሕተትን ፈጽመህ እንደነበርና ስሕተትሕን ደግመህ እንዳትፈጽም የመፍትሔህ እርምጃዎች ምን ሊሆኑ እንዲገባቸው አሰላስል፡፡ ጦምህ እንዲህ ሊሆን ይገባዋልና፡፡
ምግብ ሰውነትን እንደሚያሰባ እንዲሁ ጦም ነፍስን ከሥጋ አስተሳሰብ ተላቃ ወደ ላይ በመነጠቅ ሰማያዊ ነገሮችን ለመመርመርና ከምድራዊ ደስታ ይልቅ እጅግ ግሩም የሆነ ደስታን ለማግኘት ጥንካሬን ይሰጣታል፡፡
 አርባ ቀን ሙሉ ከምግብ ተከልክዬ ጦምኩ አትበለኝ፡፡ ይህንና ያንን አልበላሁም ወይንም ከአፌ አልገባም አትበለኝ፡፡ እኔ ይህንን ካንተ አልሻም፣ ነገር ግን ከቁጣ ርቀህ ታጋሽ መሆንህን አሳየኝ፤ ከጭካኔህ ተመልሰህ አዛኝ ወደመሆን እንደመጣህ አሳየኝ፡፡ ነገር ግን ቁጣ የሞላብህ ከሆነ ስለምን ሥጋህን በጦም በከንቱ ትጎስማታለህ ? ሰዎችን ሁሉ የምትጠላና ስስታም ከሆንክ ለአንተ ከምግብ ተከልክለህ ውሃ ብቻ መጠጣትህ ምን ትርፍ ያመጣልሃል?
ጦም እጅግ ግሩም የሆነ ነገር ነው፡፡ ኃጢአታችንን እንደማይጠቅም አረም ከውስጣችን ይነቅለዋል፡፡  እውነተኛው የጽድቅ ተክልም  በውስጣችን ልክ እንደ አበባ እንዲያብብ ይረዳዋል፡፡ (ቅዱስ ባሲልዮስ)
ጸሎት፣ ጦም ፣ትጋህ ሌሊት እና ሌሎችም አንድ ክርስቲያን የሚተገብራቸው ክርስቲያናዊ ተግባራት ምንም መልካሞች ቢሆኑ የክርስቲያናዊ ሕይወት ግቦች ግን አይደሉም፡፡ ነገር ግን ወደ ትክክለኛው ክርስቲያናዊ ሕይወት ለመድረስ የሚያገለግሉን መንፈሳዊ ትጥቆች ናቸው፡፡ትክክለኛው የክርስቲያን ግብ መንፈስ ቅዱስ በእርሱ ሰውነት ውስጥ ሥራ እንዲሠራ በመፍቀድ የመንፈስ ቅዱስ ፍሬዎችን አፍርቶ መገኘት ነው፡፡በዚህ ምድር የመንፈስ ቅዱስ ፍሬዎች ማፍራት እስካልቻልን ድረስ የእግዚአብሔርን መንግሥት መውረስ አይቻለንም፡፡ (ቅዱስ ሱራፊ)
የአዋጅ ጦም ሲገባ መንፈሳዊ የበጋ ወራቱ እንደገባ ልብ እንበል፡፡ ስለዚህም የጦር መሳሪያችንን እንወለውለው  ከእርሻቸው አዝመራውን የሚሰበሰቡትም ገበሬዎች ማጭዳቸውን ይሳሉ፤ ነጋዴዎችም በከንቱ ገንዘባቸውን ከማባከን ይከልከሉ፣ መንገደኞችም ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመግባት መንገዳቸውን ያቅኑ፡፡ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የምትወስደው ጎዳና ቀጭንና ጠባብ ናትና በጥንቃቄ እያስተዋላችሁ ተጓዙ፡፡
እንዲያው በልማድ ሰዎች እንደሚፈጽሙት ዓይነት ጦም ትጦሙ ዘንድ አልመክራችሁም፡፡ ነገር ግን ከምግብ ስለምንከለከልባት ጦም ብቻ ሳይሆን ከኃጢአት ስለምንከለከልባት  እውነተኛይቱ ስለሆነችው ጦም እጽፍላችኋለሁ፡፡ ጦም በባሕርይዋ በሕግ ካልተመራች  ለሚተገበሩዋት ሰዎች ዋጋን አታሰጥም፡፡ ስለዚህም ጦምን ለመጦም ስንዘጋጅ የጦም ዘውድ የሆነውን ነገር መዘንጋት የለብንም፡፡ ስለዚህ ስለምን ያ በእግዚአብሔር ቤተመቅደስ ደጅ ሆኖ ጸሎቱን ያደረሰው ፈሪሳዊ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስለጦሙ አንዳች ዋጋ ሳያገኝ በባዶው እጁ እንደተመለሰ መረዳት ተቀዳሚ ተግባራችን ሊሆን ይገባዋል (ሉቃ. ፲፰፥፱-፲፬(18፡9-14))፡፡ ቀራጩ አልጦመም ነገር ግን ጸሎቱ ተሰምቶለታል፡፡ ጦም ሌሎች አባሪ የሚሆኑ መልካም ሥራዎች ካልታከሉበት በቀር ልክ እንደዚኛው ፈሪሳዊ ዋጋ አያሰጠንም፡፡
ጦም ማለት መድኃኒት ማለት ናት፡፡ እንደ ሌሎቹ መድኃኒቶች ሁሉ ጦምን እንዴት እንደሚጠቀምበት የሚያውቅ ሰው ዋጋ ያገኝበታል፡፡ በጥበብ ላልተጠቀመበት ሰው ግን የማይረባና የማይጠቅም ይሆንበታል፡፡ ከጦም የሚገኘው ክብር ከምግብ በመከልከላችን ምክንያት የምናገኘው ብቻ አይደለም፡፡ ከኃጢአት ሥራዎችም ፈጽመን በመከልከላችን ምክንያት የምናገኘው ክብር ጭምር ነው ፡፡ ጦም ሰይጣን ወደ እኛ እንዳይቀርብ እንደጋሻ የሚያገልግለን መሣሪያ ነው፡፡ ነገር ግን በጦም ሰዓት ኃጢአትን ፈቅደን የምንሠራት ከሆነ ሰይጣን አጥሩን ጥሶ እንዲገባና በእኛ ላይ እንዲሠለጥን ምክንያት እየሆንነው ነው፡፡ ጦማችን ከምግብ በመከልከል ብቻ የተወሰነ ከሆነ ጦምን እናስነቅፋታለን፡፡

እየጦምክ ነውን ? መጦምህን በሥራህ ገልጠህ አሳየኝ፡፡ ድሃው እርዳታህን ፈልጎ እንደሆነ ቸርነትን አድርግለት፡፡ ጠላት ያደረግኸውን ካየኸው ከእርሱ ጋር ፈጥነህ ታረቅ፡፡ ጓደኛህ ተሳክቶለት ካየኸው በእርሱ ላይ ቅናት አይደርብህ፡፡ አፍህ ብቻ አይጡም ዐይንህም ጆሮህም እግርህም እጅህም የሰውነትህ ሕዋሳቶች ሁሉ ክፉ ከማድረግ ይጡሙ፡፡
እጆችህ ከዝርፊያና ከሕግ ውጪ ለመክበር ሲባል ትርፍን ከማጋበስ ይጡሙ፡፡ እግሮችህ የኃጢአት ሥራን ለመፈፀም ከመፋጠን ይጡሙ፡፡ ዐይኖችህም ውጫዊ በሆነ ውበት ምክንያት ከመቅበዝበዝ ይጡሙ፡፡ የሚታዩ ነገሮች ለዐይን ምግቦች ናቸው፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሔር ሕግ ጋር የሚጣረሱ ምልከታዎች ጦምን ያፈርሳሉ፡፡ነፍስንም እንድትነዋወጥ ያደርጉአታል፡፡ የምናያቸውን ነገሮች ከእግዚአብሔር ሕግ ጋር የሚስማሙ ከሆኑ ጦማችንን ያስጌጡዋታል፡፡ በጦም ምክንያት በጦም ሰዓት መመገብ የተከለከሉትን ምግቦች መመገብ የሚያስነቅፍ ከሆነ ፤ እንዴት ታዲያ በዐይናችን እንድንመለከተው በሕግ የተከለከልነውን ነገር መመልከታችን ይበልጥ አያስነቅፈን ? ምግብን ከመብላት ተከልክለሃልን? እንዲሁ ለሰውነትህ ጎጂ የሆኑ ነገሮችን በዐይንህም በጆሮህም ከመመገብ ተከልከል፡፡ ጆሮ የምትጦመው ለኃጢአት ከሚጋብዙ ክፉ ወሬዎችና ሐሜትን ከመስማት ነው፡፡ “ሐሰተኛ ወሬን አትቀበል ሐሰተኛ ምስክርም ትሆን ዘንድ ከኃጢአተኛ ጋር እጅህን አታንሣ፡፡”እንዲል(ዘጸአ.፳፫፥፩(23፡1))
አፍህም ከከንቱ ንግግር ይጡም ፡፡ ከአሣና በጦም ሰዓት መመገብ ከተከለከልናቸው የፍስክ ምግቦች ተከልክለን ወንድሞቻችንንና እኅቶቻችንን በክፉ ቃላችን ሕሊናቸውን የምናቆስልና በሐሜት ሥጋቸውን የምንበላ ከሆነ ከጦማችን ምን ዋጋን እናገኛለን? ክፉ ተናጋሪ የወንድሙን አካል ያቆስላል ሥጋውንም ይበላል፡፡ ስለዚህም ቅዱስ ጳውሎስ ይህን አስመልክቶ  እጅግ የሚያስደነግጥ ንግግርን ተናገረ “ሕግ ሁሉ በአንድ ቃል ይፈጸማልና እርሱም፡- ባልንጀራህም እንደ ራስህ ውደድ  የሚል ነው፡፡ ነገር ግን እርስ በእርሳችሁ ብትነካከሱና ብትበላሉ እርስ በእርሳችሁ እንዳትጠፋፉ ተጠንቀቁ፡፡(ገላ.፭፥፲፭(5፡15))ብሎ አስጠነቀቀን፡፡
ስለታሙ የሐሜት ጥርስህ የሚያርፈው በወንድምህ ሥጋ ላይ ሳይሆን ነፍስ ላይ ነው፡፡ በዚህም ጥርስህ ወንድምህን በእጅጉ ትጎዳዋለህ፡፡ እንዲህ በማድረግህ አንተም እርሱንም ሌሎችንም ብዙ ሺህ ጊዜ ትጎዳቸዋለህ፡፡ በሐሜትህ አንተን የሚሰማህ ባልንጀራህ የሐሜት ተባባሪ ይሆናል፡፡ በዚህም ምክንያት እርሱንም በደለኛ ታደርገዋለህ፡፡ እርሱም በእርሱ ላይ ከነገሠበት ኃጢአት የተነሣ ለሌላ ለወዳጁ ምን መርጦ ማውራት እንዳለበት ሳያውቅ ከሐሜተኞች ጎራ ይቀላቀላል፡፡እንዲህ ዓይነት ሰው ጻድቅ ልንለው እንችላለንን? እንዲህ ዓይነት ሰው  በመጦሙ ትልቅ የጽድቅ ሥራን እንደፈጸመ ቆጥሮ ይኩራራል፡፡ ሰዎችን ወደ ኃጢአት እየመራ ትልቅ ሥራን እንደሠራ ሰው ራሱን በከንቱ ያስኮፍሳል፡፡ ከዚህ ጎን ለጎን ሊታይ የሚገባው ትልቁ ቁም ነገር ስለቤተክርስቲያን ጥቅም ሲባል የእንዲህ ዓይነቱን ሰው ንግግር ከመስማት መከልከል እንደሚገባ ነው፡፡ ምክንያቱም የዚህ ሐሜተኛ ወሬ እርሱን ብቻ ኃጢአተኛ የሚያሰኝ ጉዳይ ሳይሆን ቤተክርስቲያንንም ጭምር የሚያሰድብ ነውና፡፡
ስለዚህ በጦም ሰዓታችሁ ጊዜም ይሁን አይሁን  ሦስት ነገሮችን በሕሊናችሁ ትይዙ ዘንድ እመክራችኋለሁ፡፡ እነርሱም ክፉ ከመናገር መከልከልን፣ ማንንም ሰው እንደጠላት ከማየት መቆጠብንና እንደልምድ አድርጋችሁ ከያዛችሁት መሐላ ትርቁ ዘንድ እመክራቸኋለሁ፡፡
በአጨዳ ላይ ያለ ገበሬ እህሉን ከእርሻው ላይ በአንዴ እንዳይሰበስብ ነገር ግን ጥቂት በጥቂት እንዲሰበስብ እኛም እነዚህን ምክሮች ተግባራዊ በማድረግ በዚህ የጦም  ወቅት ልንለማመዳቸው እና መልካም ልምዶቻችን ልናደርጋቸው ይገባናል፡፡ እንዲህም በማድረጋችን በቀላሉ መንፈሳዊ ጥበብን ገንዘባችን ማድረግ ይቻለናል፡፡ በዚህም ዓለም ሳለን መልካም ተስፋ ያለውን አዝመራ እናፈራለን፡፡በሚመጣውም ዓለም በክርስቶስ ፊት ያለፍርሃት በደስታ ተሞልተን እንድንቆም ይረዱናል፡፡ ለእግዚአብሔር መንግሥት የሚያበቃንን ጸጋ አግኝተን የክብሩ ወራሾች ያድርገን፤ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ክብር ምስጋና ይሁን ዛሬም ዘወትርም እስከዘላለሙ አሜን፡፡
 ጦም የጤንነት እናት፣ የፍቅር እኅት፣ የትሕትና ወዳጅ ናት፡፡ ሕመሞች አብዛኛውን ጊዜ ያለቅጥ ከመመገብ የሚመነጩ ናቸው፡፡ (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)
ከምግባራት ሁሉ ታላቁ ጸሎት ነው ነገር ግን የእርሱ መሠረቱ ጦም ነው፡፡የምንጦምበት ምክንያት ርኩስ የሆነውን የሰይጣንን መንፈስ በነፍሳችን ውስጥ እንዳያድር ለመጠበቅ ነው፡፡ ሥጋችንን ለጦም ባስገዛነው ጊዜ ነፍሳችን ነፃነትን፤ ጥንካሬን ሰላምን ፣ንጽሕናን እንዲሁም እውቀትን ለመለየት እንድትበቃ ትሆናለች፡፡ (ጻድቁ ዮሐንስ ዘክሮስታንድ)
እውነተኛ ጦዋሚ ራሱን ከክፉ ምግባራት የከለከለ፤ ከንቱ የሆኑ ንግግሮችን ከመናገር የተቆጠበ፣ ሐሰትን የማይናገር፣ ሐሜተኛ ያልሆነ፣ በማንም ላይ የማይፈርድ፣ሽንገላን የማይወድና እኒህንም ከመሰሉ ነገሮች ራሱን የተጠበቀ ፣የማይቆጣ፣ የማይበሳጭ ፣ተንኮለኛ ያልሆነ ፣ ቂመኛ ያልሆነና፣ እነዚህን ከመሳሰሉ ክፋቶች ሁሉ የራቀ ሰው ነው፡፡
ሕሊናህ ኃጢአትን  ከማሰብ ይጡም፡ አእምሮህም ኃጢአትን ከማስታወስ ይከልከል፡፡ ክፉን ከመመኘት ሁሉ ጡም፡፡ ዐይኖችህ ከንቱ የሆኑ ነገሮችን ከመመልከት፣ ጆሮህም ከንቱ ከሆኑ ዘፈኖችና ከሐሜተኞች ሹክሹክታዎች ጠብቅ፡፡ አንደበትህ ከሐሜት፣ በሌላው ላይ ከመፍረድ ፣ከስድብ፣ ከውሸት ፣ከማታለል፣ከሽንገላ ንግግሮች እንዲሁም ከማይጠቅሙና አጸያፊ ከሆኑ  ቃላት ይጡሙ፡፡ እጆችህም ሰውን ከመግደልና የሌላውን ንብረት ከመዝረፍ ይጡሙ፡፡ እግሮችህም ኃጢአትን ለመፈጸም ከመሄድ ይጡሙ፡፡ ከክፉ ተመለስ መልካምንም ፈጽም፡፡ (ቅዱስ ኤፍሬም)
 ጦም ምን እንደሚያደርግ ትመለከታለህን? ሕመምን ይፈውሳል ፣አጋንንትን ያስወጣል፣ ክፉ አሳቦችን ከአእምሮ ያስወግዳቸዋል፣ ልብንም ንጹሕ ያደርጋታል፡፡ አንድ ሰው በክፉ መንፈስ የተያዘ ቢሆን  እንዲህ ዐይነት መንፈስ በጦምና በጸሎት እንደሚወጣ ያስተውል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ይህ ዓይነት ግን ከጸሎትና ከጦም በቀር አይወጣም” እንዳለው (ማቴ. ፲፯፥፳፩(17፡21)) (ቅዱስ ቲክሆን)
የአርባ ቀን ጦም የሥጋ ፍትወታትን ይገድላቸዋል፣ቁጣንና ብስጭትን ከሰውነታችን ያስወግዳቸዋል፣  ከሆዳምነት ከሚመነጩ የትኞቹም ነገሮች ሁሉ ነፃ ያወጣናል፡፡ በበጋ ወራት ፀሐይ ከነሙሉ ኃይሉዋ እንድትወጣና ምድርንም በሙቀቱዋ እንደምታግል በላዩዋም የበቀሉ አትክልቶችን እንደምታደርቅ፤ ከሰሜን የሚነፍሰውም ነፋስ የደረቁትን ሳሮች እንደሚጠርጋቸው፤  እንዲሁ በጦም ወቅትም አብዝቶ በመመገብ የበቀሉትን የሥጋ ፍትወታት ይወገዳሉ፡፡ (ቅዱስ አትናቴዎስ)
ቅዱሳን ጠዋሚዎች ጽኑ ወደሆነው የጦም ሥርዓት የገቡት ወዲያው አይደለም፡፡  በጥቂት ምግብ ወደ መጥገብ የመጡት ቀስ በቀስ ነው፡፡ እነዚህ ቅዱሳን ኃጢአትን ፈጽመው አያውቋትም፡፡ ሁልጊዜ ለመልካም ሥራ እንደተፋጠኑ ነው፡፡ በእነርሱ ዘንድ ሕመም አይታወቅም እድሜአቸውም  ከሰው ሁሉ በተለየ የረዘመ ነው፡፡ (ቅዱስ አግናጢዎስ)
ጦም  የሰውን እድሜ አያሳጥርም ፣ ቅዱስ ቄርሎስ ዘአንኮራይት በ108 እድሜው አረፈ፡፡ ቅዱስ እንጦስም 105 ዓመት ሙሉ ኖሮአል፡፡ ቅዱስ መቃርስ ዘእስክንድሪያ የኖረበት እድሜ 100 ዓመት ነበር ፡፡ (ቅዱስ አውግስጢኖስ)
አርባውን ቀን መጦምን ቸል አትበሉ፡፡ ምክንያቱም ክርስቶስን የምንመስልበት ሕይወት ከዚህ ጦም እናገኛለንና፡፡ (ቅዱስ እንጦስ)
ወስብሐት ለእግዚአብሔር 
Source: eotc-mkidusan.org

ስሞት እጸልይላችኋለሁ

በዲ/ን ሄኖክ ኃይሌ

“ከመውጣቴም በኋላ እነዚህን ነገሮች እንድታስቡ በየጊዜው ትችሉ ዘንድ እተጋለሁ!”2ኛ ጴጥ.1÷13-15

ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም በመጣበት ወቅት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን መሥርቶአል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያቱን “እኔን ማን ትሉኛላችሁ?” ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ “አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ” ብሎ ቅዱስ ጴጥሮስ መልሶ ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ “አንተ ዓለት ነህ በዚህችም ዓለት ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ፤ የሲኦልም ደጆች ሊያናውጿት አይችሉም፡፡” በማለት ቤተ ክርስቲያንን በሐዋርያት መሠረት ላይ መሠረተ/ማቴ.16÷16-18/፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ በአምሳ አምስት ዓመቱ ወደ ሐዋርያት የተጠራ፣ በሁሉም ስፍራ በሐዋርያት ስም ዝርዝርም፣ መልስ በመስጠትም፣ በመካድም፣ ንስሓ በመግባትም ፈጣን እንደነበር ቅድመ ትንሣኤ ክርስቶስ የተጻፈው ታሪኩ ያስረዳል፡፡ ከትንሣኤ በኋላ ሦስት ጊዜ ክዶት መጸጸቱን የተመለከተለት ጌታ አንዳች የሚቆጠቁጥ የወቀሳ ቃል ሳይኖረው በጭቃ ላይ የወደቀ ዕንቁን ወልውለው ወደ ቦታው አንደሚያስቀምጡት ወደ ክብር ስፍራው መለሰው፡፡ አልፎ ተርፎም ለምሕረቱ ወሰን የሌለው አምላክ ይህን ሐዋርያ “ ግልገሎቼን አሰማራ፣ ጠቦቶቼን ጠብቅ፣ በጎቼን አሰማራ” ብሎ ምእመናንን ከሕፃናት እስከ አረጋውያን አደራ ሰጠው /ዮሐ.21÷15-17/፡፡ቅዱስ ጴጥሮስ ጸጋ መንፈስ ቅዱስን በተቀበለበት ዕለት በአንድ ቀን ሦስት ሺህ ነፍሳትን በትምህርቱ ማርኮ “ምን እናድርግ?” በማሰኘት ጠብቅ አሰማራ የተባለውን መንጋ ወደ በረቱ ማስገባት ጀመረ፡፡ /ሐዋ.2÷31/ በሐዋርያዊ አገልግሎቱ ምእመናንን በአፍም በመጽሐፍም ሲያስተምር ቆይቷል፡፡ በኋላም ጠብቃቸውና አሠማራቸው የተባለውን ግልገሎች፣ ጠቦቶችና በጎች ሲጠብቅና ሲያሠማራ ከተኩላ ታግሎ ነፍሱን ሰጠ፡፡ የእረኝነት ሥራውን ሊፈጽም ቁልቁል ተሰቅሎ “የእረኞች አለቃ” /1ኛጴጥ.5÷4/ ብሎ በመልእክቱ የጠራውን የጌታውን ፈቃድ ፈጸመ፡፡

ይህ ሐዋርያ በመልእክታቱ ምእመናንን ሲገሥጽና ሲመክር ሲያስተምር የኖረ ሲሆን በሁለተኛይቱ መልእክቱ ላይ ግን ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነ ኃይለ ቃልን ጽፏል፡፡ “ስለዚህ እነዚህን ነገሮች ምንም ብታውቁ በእናንተም ዘንድ ባለ እውነት ብትጸኑ ስለ እነዚህ ዘወትር እንዳሳስባችሁ ቸል አልልም፡፡ ሁል ጊዜም በዚህ ማደሪያ ሳለሁ በማሳሰቤ ላነቃችሁ የሚገባኝ ይመስለኛል፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳመለከተኝ ከዚህ ማደሪያዬ መለየቴ ፈጥኖ እንዲሆን አውቃለሁና፡፡ ከመውጣቴም በኋላ እነዚህን ነገሮች እንድታስቡ በየጊዜው ትችሉ ዘንድ እተጋለሁ” /2ኛጴጥ. 1÷13-15/

ብታውቁም፤ ብተጸኑም ማሳሰቤን ቸል አልልም!

ቅዱስ ጴጥሮስ በመልእክታቱ ስለ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነትና ስለ ሰው ልጅ ብሎ ስለተቀበለው መከራ፣ ክርስቲያኖች ሊኖራቸው ስለሚገባ መንፈሳዊ አኗኗር፣ አለባበስ፣ ስለ ጋብቻና ቤተሰባዊ ጉዳዮች፣ በምእመናን ላይ ስለሚመጡ መከራዎችና የዲያብሎስ ውጊያዎች፣ ድል ሲያደርጉም ስለሚያገኙት ጸጋና ዋጋ፣ ስለሚደርሱበት መዓርግ በአጠቃላይ በቀላሉ ተዘርዝሮ የማያልቅ ሰፊ ትምህርትን በመልእክቱ አስተምሯል፡፡ ይሁንና ሐዋርያው አውቀውታል፣ ጸንተዋል ብሎ ማሳሰቡን አላቆመም፡፡ ሰው ከመንገድ የሚስተው በእውቀት ጉድለት ብቻ አይደለም፡፡ እያወቁ መሳት፣ ጸናሁ ሲሉም መጥፋት አለ፡፡ ስለዚህም “አሳስባችሁ ዘንድ ቸል አልልም፡፡” አለ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ መንጋውን ጠብቅና አሰማራ የተባውን አደራ የማይረሳ፣ በጥበቃ ተሰላችቶ ቸል የማይል፣ ትናንት የበሉት የጠጡት ይበቃቸዋል የማይል በመሆኑ ያውቁታል ብሎ ከመናገር ሳይቆጠብ “ዘወትር እንዳሳስባችሁ ቸል አልልም፡፡” አለ፡፡

በዚህ ማደሪያ ሳለሁ!

ሥጋ የነፍስ ማደሪያ ናት፤ አዳሪዋ ነፍስ ከማደሪያዋ ሥጋ ስተለይ ሰው ያን ጊዜ ሞተ ይባላል፡፡ “ከነፍስ የተለየ ሥጋ የሞተ ነው” እንዲል /ያዕ.2÷26/ ጻድቁ ኢዮብም “ይህ ቁርበቴም ከጠፋ በኋላ÷ በዚያን ጊዜ ከሥጋዬ ተለይቼ እግዚአብሔርን እንዳይ አውቃለሁ፡፡” ኢዮ.19÷26/ ያለው ሥጋ ጊዜያዊ ማደሪያ መሆኑን ሲያስረዳና ራሱን ከነፍስ አንጻር አድርጎ በሞት ሥጋውን ጥሎ እንደሚሄድ ሲናገር ነበር፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ “በዚህ ማደሪያዬ ሳለሁ በማሳሰቤ ላነቃችሁ ይገባኛል፡፡” ሲል በሥጋዬ ሳለሁ፣ ነፍሴ ሳትወሰድ ማለቱ ነበር፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስን ቀሪ ዕድሜውን በችኮላ የሚጠቀመው ለሌላ ሥጋዊ ተርታ ጉዳዮች ሳይሆን ምእመናን ያስተማረውን ትምህርት እንዳይገድፍና አንዳይጠፉበት በማሳሰብ ማንቃት ነው፡፡


ጌታዬ እንዳመለከተኝ መለየቴ ፈጥኖ እንዲሆን አውቃለሁ!

“በእግዚአብሔር ፊት የቅዱሳኑ ሞት የከበረ” ስለሆነ ሞት ለቅዱሳን ድንገተኛና ያልተጠበቀ አይሆንባቸውም፡፡ እርግጥ ነው ሰው ሁሉ ሟች እንደ ሆኑና የሞትን አይቀሬነት በመጥቀስ ሁሉም ሰው እንደሚሞት ያውቃል ሊባል ይችላል፡፡ ቅዱሳን ግን የሚሞቱ መሆናቸውን የሚያውቁት ሞት አይቀርም ብለው ሳይሆን የሚሞቱበትን ጊዜና ሁኔታ ለመረጣቸው ለባሪያዎቹ የሚያደርገውን የማይሠውር እግዚአብሔር ገልጣላቸው ነው፡፡ የሚከተሉት የሊቀ ነቢያት ሙሴንና የቅዱስ ጳውሎስን ንግግሮች እንመልከት፡-

“እኔ ግን በዚህች ምድር እሞታለሁ ዮርዳኖስንም አልሻገርም” /ዘዳ.4÷22/

“በመሥዋዕት እንደሚደረግ የእኔ ሕይወት ይሠዋልና የምሄድበትም ጊዜ ደርሷል” /2ኛጢሞ.4÷6/

እነዚህ ታላላቅ ቅዱሳን የሚሞቱ መሆናቸቸውን ብቻ ሳይሆን የሚሞቱበትን ቦታ ጊዜ አስቀድመው መናገራቸው ከእግዚአብሔር ስለተነገራቸው ነው፡፡ የቅዱሳን አባቶቻችንን እና የቅዱሳት እናቶቻችንን ገድላት ስንመረምር ቅዱሳን ዕለተ እረፍታቸው ቀድሞ በእግዚአብሔር እንደሚነገራቸው እንረዳለን፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም ሰው እንደመሆኑ “መሬት ነህና ወደ መሬት ትመለሳለህ” ብሎ ጌታ ለሁሉ ካመለከተው ጥሪ በተጨማሪ ከቅዱሳን አንዱ እንደመሆኑ ከመሞቱ በፊት እንደሚሞት ያውቅ ነበር፡፡ ጌታችን ከዕርገቱ በፊትና ከዕርገቱ በኋላ ሁለት ጊዜ ተገልጦ ስለሞቱ ነግሮታል፡፡

ከዕርገቱ በፊት ከላይ የጠቀስነውን የእረኝነት አደራ ከሰጠው በኋላ “እውነት እውነት እልሃለሁ አንተ ጎልማሳ ሳለህ ወገብህን በገዛ ራስህ ታጥቀህ ወደምትወደው ትሄድ ነበር፤ ነገር ግን በሸመገልህ ጊዜ እጆችህን ትዘረጋለህ ሌላውም ያስታጥቅሃል ወደማትወደውም ይወስድሃል፡፡” ብሎታል፡፡ ወንጌልን ጽፎ በብዙ ቦታዎች የጻፈውን ሲተረጉምና ሲያትት የምናገኘው ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ትርጓሜን ሳንሻ ንባቡ ላይ “በምን ዓይነት ሞት  እግዚአብሔርን ያከብር ዘንድ እንዳለው ሲያመለክት ይህን አለ፡፡” ብሎ የጌታን ንግግር ትርጓሜ አስከትሎ ጽፎልናል፡፡

በእርግጥም ቅዱስ ጴጥሮስ በሸመገለ ጊዜ እጆቹን በተዘቀዘቀ መስቀል ላይ ዘርግቶ ቁልቁል መሰቀል ትንቢተ ክርስቶስን ፈጽሟል፡፡

ጌታችን ከዐረገ በኋላ ደግሞ ቅዱስ ጴጥሮስ በሮም ሲያስተምር “ልበ ንጹሖች ብጹዓን ናቸው፡፡” ብሎ ባስተማረው ትምህርት ሚስቶቻችንን አሸፈተብን ያሉ ሰዎች ተነሡበት፡፡ በዚህን ወቅት ሴቶቹ ተማክረው ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲሸሽ ነገሩት ከከተማይቱ ወጥቶ ሊሄድ ሲል ጌታችን ተገልጦ ታየው “ጌታ ሆይ ወዴት ትሄደለህ” ቢለው “ዳግም በሮም ልሰቀል” በማለት ነገረው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ በዚህ ልቡ ተነክቶ ወደ ሮም ተመለሰና የሰማዕትነትን አክሊል ተቀዳጀ፡፡ “ጌታችን እንዳመለከተኝ” ያለው ይህን ነበር፡፡

ከመውጣቴም በኋላ አንድታስቡ በየጊዜው ትችሉ ዘንድ እተጋለሁ!

ከላይ የተመለከትናቸው ሃሳቦች ቅዱስ ጴጥሮስ ጊዜ ሞቱ እንደቀረበ አውቆ መናገሩን እና ምእመናን የተማሩትን በማሳሰብ ሲያነቃቸው እንደነበር የሚያስረዱ ናቸው፡፡ እስካሁን የተመለከትናቸው የሚያወሱት ይህ ሐዋርያት በሕይወት ሳለ ስለሚያደርጋቸው ነገር ነበር፡፡ በመጨረሻው ዐረፍተ ነገር ግን “ከመውጣቴ በኋላ የሚል ሐረግ እናገኛለን፡፡ “ከመውጣቴ በኋላ” ሲል ምን ማለቱ ነው?

ቀደም ባሉት ዐረፍተ ነገሮች እንደሚሞትና ይህንንም ጌታችን እንዳመለከተው ተናግሮ ነበር፡፡ ስለዚህ መውጣቴ ያለው ሞቱን እንደ ሆነ እሙን ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ሞት መውጣት ተብሎ ሲነገር የቅዱስ ጴጥሮስ የመጀመሪያ አይደለም፡፡ በታቦር ተራራ ከሙሴና ኤልያስ ጋር ስለመነጋገሩ በተጻፈበት ስፍራ “በክብርም ታይተው በኢየሩሳሌም ሊፈጽም ስላለው ስለ መውጣቱ ይናገሩ ነበር” ይላል፡፡ በኢየሩሳሌም የተፈጸመው መውጣቱ ደግሞ ሞቱ ነው፡፡ /ሉቃ.9÷31/ ስለዚህ ቅዱስ ጴጥሮስ ባስተማርኳችሁ እንድትጸኑ “ከሞትኩም በኋላ እተጋለሁ!” እያለ ነው፡፡ “ከሞትኩ በኋላ” የሚለውን እናቆየውና “እተጋለሁ!” የሚለውን ቃል በጥቂቱ እናብራራው፡፡

ትጋት ምንድርን ነው? ትጋት አንድ ነገር ያለማቋረጥ፣ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ፣ ያለመታከት ማድረግ ነው፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን “ታካች ሰው ምንም አደን አያድንም፤ የሰው የከበረ ሀብቱ ትጋት ነው” በማለት ትጋት የታካችነት ተቃራኒ መሆኑንና ጥቅሙን ተናግሯል /ምሳ.12÷27/፡፡ ጌታችን በምሴተ ሐሙስ ቅዱሳን ሐዋርያቱን “ከእኔ ጋር አንዲት ሰዓት እንኳን ልትተጉ አልቻላችሁምን? ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ” ብሎ ገሥጿቸው ነበር /ማቴ.26÷30/፡፡ ጸጋ መንፈስ ቅዱስን ከተቀበሉ በኋላ ግን ሐዋርያት ትጉሐን ነበሩ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንደ መሰከረላቸው “ወደዚህም ወደ ተሰፋ ቃል አሥራ ሁለቱ ወገኖቻችን ሌሊትና ቀን በትጋት እያመለኩ ይደርሱ ዘንድ አለኝታ አላቸው” /ሐዋ.26÷7/ በዚህ ሁሉ ትጋት አለመታከት፣ አንድን ነገር ሌሊትና ቀን ማድረግ መሆኑን ተረዳን፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ “ከመውጣቴም በኋላ እነዚህን ነገሮች እንድታስቡ በየጊዜው ትችሉ ዘንድ እተጋለሁ” ሲል የሚተጋው በምንድርን ነው? እየዞረ በማስተማር ይሆን? ይህማ ቢሆን ከመሄዴ በፊት  ላሳስባችሁ ባላለን ነበር፡፡ ደግሞም ማስተማሩን በሚገባ ፈጽሞ በሰማዕትነት አርፏል፡፡ ታዲያ ከሞተ ወዲያ የሚተጋው ምን በማድረግ ነው? የትስ ነው የሚተጋው? መቼስ በመቃብር ያለሥጋው ሊተጋ አይችልም፡፡ “የሞቱትስ ተነሥተው ያመሰግኑሃልን? በመቃብርስ ውስጥ ቸርነትህን ይናገራሉን?” ብሏል ቅዱስ ዳዊት /መዝ.87÷15/ ራሱ ቅዱስ ጴጥሮስም “ከማደሪያዬ እለያለሁ፡፡ ብሎ ከሞተ ወዲያ እኔ የሚላት ነፍሱን እንደሆነ አስረድቶናል፡፡ ታዲያ በነፍሱ በሰማይ ምን እያደረገ ይሆን የሚተጋው? መቼስ በሰማይ እርሻ ቁፋሮ፣ ጽሕፈት፣ ድጒሰት የለም፡፡ ሐዋርያው በምን ይሆን የሚተጋው? በጸሎት ነዋ!

ስለዚህ ቅዱስ ጴጥሮስ “እንደተማራችሁት መኖርን እንዳትዘነጉ በየጊዜው /አንድ ጊዜ ብናስብ አንድ ጊዜ መዘንጋት አለና/ ትችሉ ዘንድ ከሞትኩም በኋላ ያለማቋረጥ ያለመሰልቸት ስለ እናንተ በመጸለይ እተጋለሁ! ማስተማርና መልእክትን ጽፎ መተው ብቻ ሳይሆን በተማራችሁት መገኘት እንድትችሉ በአጸደ ነፍስም ብሆን እለምናለሁ፣ እማልዳለሁ! እያለ ነው፡፡

በቅዱስ ጴጥሮስ ዓለትነት የተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በአደባባይ ስለእርሷ የተጻፋላት፣ በደሙ የዋጃት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሷ ነው፡፡ እርሱ በሁሉ የሞላ ሲሆን “ሁሉን በሁሉ ለሚሞላ ለእርሱ ሙላቱ የሆነች” አካሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት /ኤፌ.1÷22/፡፡ ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ አካሉ ስትሆን ክርስቶስ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ራሷ ነው፡፡ እኛ ደግሞ የሰውነት አካል ክፍሎች ነን፡፡ “እንግዲህ እናንተ የክርስቶስ አካሉ ናችሁ፤ እያንዳንዳችሁ የአካሉ ክፍሎች ናችሁ፡፡” ተብለናል /1ኛቆሮ.12÷27/፡፡ በቤተ ክርስቲያን ሕይወትን የሚሰጡ ጥምቀትን፣ ንስሐን፣ ቊርባንን የመሳሰሉ ምስጢራትን በመፈጸም ራሳችን ከሆነው ከመድኃኔዓለም ጋር አንድ እንሆናለን፡፡

ክርስቲያኖች ሲሞቱ ከዚህ ኅብረት ይነጠላሉ ማለት አይደለም፡፡ ራሷ ክርስቶስ በሰማይም በምድርም ስላለ ቤተ ክርስቲያንም በምድርም በሰማይም አለች፡፡ ስለዚህ አንድ ክርስቲያን ነፍሱ ከሥጋው ስትለይ ወደ ሰማያዊቱ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ይሄዳል፡፡ የሰማይዋ ቤተ ክርስቲያን ደግሞ ድል በነሱ ቅዱሳን የተሞላች ፍጹም መንፈሳዊ የሆነ ሥርዓት ያለባት፣ ሥጋዊ ደማዊ አሳብ የማይሰለጥንባት ናት፡፡ ከእኛ ተለይተው ወደዚያ ኅብረት የተደመሩ ወገኖቻችን በላይ ያሉ የክርስቶስ አካላት ናቸው፡፡ ከእኛ በምድር ካለነው የክርስቶስ አካላት ጋር አንድነታቸው አይቋረጥም፡፡ የክርስቶስ አካል አይከፈልማ! ስለዚህ በሰማይ ካሉት ድል የነሡ ቅዱሳን ጋር እኛ ደካሞቹ በጸሎት እንገናኛለን፡፡

“ዐይን እጅን አልፈልግሽም ልትላት አትችልም፤ ደካሞች የሚመስሉህ የአካል ክፍሎች ይልቁንም የሚያስፈልጉህ ናቸው፡፡ ተብሎ እንደተነገረ እኛ ኃጢአተኞቹ የቤተ ክርስቲያን የአካል ክፍሎች ብንሆንም ቅዱሳኑ ስለ እኛ ይጸልያሉ /1ቆሮ.12÷21/፡፡ ምክንያቱም ደካማ ብንሆንም ለቅዱሳን እናስፈልጋቸዋለን፡፡ ቅዱሳን ኃጥአንን ካልወደዱ ቅድስናቸውን ያጣሉ፡፡ እኛን ካልወደዱ “እኔ ክርስቶስን እንደመሰልሁ እናንተም እኔን ምሰሉ” “አሁን እኔ ሕያው ሆኜ አልኖርም፤ ክርስቶስ ግን በእኔ ይኖራል፡፡” ብለው ለመናገር እንደምን ይችላሉ? /ገላ.2÷20/

እኛ በሥጋ ድሆች የሆኑ ነዳያንን በመመጽወት እንደምንከብር ቅዱሳንም በነፍስ ድሆች የሆንን እኛን በአማላጅነት ጸሎታቸው እየመጸወቱ ይከብራሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ “ለድሀ ግን የሚራራ ምስጉን ነው፡፡” ይላልና በምግባር ድሆች ለሆንን ለእኛ መራራት የቅዱሳን ግብር ነው፡፡ “ጻድቅ ሰው ለእንስሳው ነፍስ ይራራል” ተብሎ እንደተነገረላቸው ቅዱሳን ክቡር ሆነን ሳለን ለማናውቅ እንደሚጠፉ እንስሶች ለመሰልን ለእኛ ለኃጢአተኞች ይራራሉ፤ ይማልዱማል /ምሳ.12÷10፣ 14÷21/፡፡

ቅዱሳን በሕይወተ ሥጋ እያሉ መከራን ታግሠው ስለ ሌሎች በደል ይለምናሉ፡፡ ሳይበድሉ ራሳቸውን በኃጢአትኛው ቦታ አርገው፣ ከደካሞች ጋር እንደ ደካማ ሆነው ይማልዳሉ፡፡ ታዲያ ነፍሳቸው ከሥጋቸው ተለይታ “ሲሄዱና ከክርስቶስ ጋር ሲኖሩ” /ፊል.1÷23/ ምንኛ ይለምኑ ይሆን?

በምድር ያለችው ቤተ ክርስቲያን በሕይወተ ሥጋ ለሌሉና ወደ ሰማዩ ኅብረት ለሄዱ ምእመናን ጸሎተ ፍትሐትን፣ መታሰቢያን በማድረግ፤ ለዚያ የሚያበቃ ቅድስና ያላቸውን ደግሞ በዓላቸውን በማክበር ታስባቸዋለች /2ጢሞ.1÷17-18/፡፡ በሰማይ ያሉት ቅዱሳን ደግሞ ቅዱስ ጴጥሮስ እንዳለው ስለ እኛ ይተጋሉ፡፡ የቤተ ክርስቲያንን መከራና የምእመናንን ስቃይም በዝምታ አይመለከቱም፡፡ በዙፋኑ ፊት ቆመው “ቅዱስና እውነተኛ ጌታ ሆይ እስከ መቼ ድረስ አትፈርድም? ስለ ደማችንስ በምድር በሚኖሩት ላይ እስከ መቼ አትበቀልም?” እያሉ ያማልዳሉ፡፡ /ራእ.6÷10/ የቅዱስ ጴጥሮስ በረከቱ አይለየን! አሜን፡፡

/ምንጭ፡ ሐመር  ሐምሌ 2002 ዓ.ም./
Source: eotc-mkidusan.org

መንፈሳዊ ተጋድሎ

በዲ/ን አሉላ መብራቱ
1.    መንፈሳዊ ተጋድሎ ማለት ምን ማለት ነው?

መንፈሳዊ ተጋድሎ ማለት - አንድ ሰው የሚያምንበትን እምነት፣ የሚመራበትን ሕግ፣ የሚያልመውን ተስፋ እና የሚወደውን ነገር ተከትሎ ከግቡ ለመድረስ ማድረግ ያለበትን በማድረግ÷ ማድረግ የሌለበትን በመተው በነፃ ፈቃዱ ወስኖ፥ በሙሉ ልቡናው፥ በሙሉ ኃይሉ የሚያደርገው የውስጥና የውጭ መንፈሳዊ እንቅስቃሴ፥ ጥረትና ትግል ነው፡፡
 
ሀ. ከፈቃደ ሥጋ ጋር የሚደረግ ውጊያ ነው፡፡
ሰው በዚህ ዓለም በተሰጠው ዘመኑ ራሱን ለፈጣሪው ለማስገዛት ከራሱ ጋር ብርቱ ተጋድሎ ማድረግ ግድ ይለዋል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ሥጋ በመንፈስ ላይ መንፈስም በሥጋ ላይ ይመኛል፤ እነዚህም እርስ በርሳቸው ይቀዋወማሉ፡፡ ስለዚህም የምትወዱትን ልታደርጉ አትችሉም›› ብሎ የገለጸው ይህንን በሰው ሕይወት ውስጥ ያለውን የማያቋርጥ ጦርነት ነው፡፡ (ገላ 5፥12) ታላቁ አባት ኢዮብም ‹‹በምድር ላይ የሰው ሕይወት ብርቱ ሰልፍ አይደለምን ?›› በማለት ሰው ጽኑ ጦርነት የሚካሄድበት የጦር ሜዳ መሆኑን ገልጿአል፡፡ ይህም ጦርነት በተወሰነ ጊዜ ተነሥቶ የሚጠፋ ሳይሆን በሰው ዘመን ሁሉ የሚኖርና የዕድሜ ልክ ትግል ነው፡፡ ይህን የሥጋና የነፍስ ጦርነት በነፍስ አሸናፊነት ማጠናቀቅና ፈቃደ ሥጋን ድል አድርጎ ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛት ይገባል፡፡
ይህ ሲባል ግን ሥጋ ርኵስ ነው፤ ሥጋ መጥፋትና መወገድ አለበት ማለት አይደለም፡፡ ሥጋ በራሱ ርኵስ አይደለምና፤ ምክንያቱም ሥጋ የተፈጠረው በራሱ በእግዚአብሔር ነው፡፡ አምላካችን ደግሞ ርኵስ ነገር አይፈጥርም፡፡ ሰውን (ሰው የነፍስና የሥጋ ተዋሕዶ ውጤት ነው) ከፈጠረ በኋላ ‹‹ያደረገውን ሁሉ አየ እነሆም እጅግ መልካም ነበረ፡፡›› ተብሏል፡፡ (ዘፍ1፥31) ሥጋ ርኵስ ቢሆን ኖሮ እግዚአብሔር ወልድ (ቃል) ‹‹ሥጋ ሆነ›› ባልተባለ ነበር፡፡ (ዮሐ 1፥14) አዳምና ሔዋን ከኃጢአት በንጽሕና ይኖሩ ነበር፡፡ ‹‹አዳምና ሚስቱ ሁለቱም ዕራቁታቸውን ነበሩ፣ አይተፋፈሩም ነበር›› እንዲል (ዘፍ 2፥25)  ህፃናት፣ ልጆች  ሰውነት አላቸው ነገር ግን የኃጢአት ምኞት የላቸውም፡፡
ስለዚህ ፈቃደ ሥጋን መዋጋት ማለት ሥጋን ማጥፋት ወይም ደግሞ ተፈጥሮአዊና ንጹህ የሆነ የሥጋን ፈቃድ ማስወገድ ማለት ሳይሆን፣ ኃጢአትን በማየት፣ በመስማት፣  በመለማመድ ያደገውን÷ ወደ ኃጢአት ያዘነበለውን ፈቃዳችንን መጐሰም/መግራት ማለት ነው፡፡ ይህ ፈቃድ (ኃጢአት) ሥጋን በመጠቀም ይሠራል÷ ሥጋን ከነፍስ ቁጥጥር ውጭ እንዲሆን ያደርገዋል፡፡
የሰው ሥጋዊ ባሕርዩ ምግብ ሲያጣ ይራባል፣ ይደክማል፣ ሥራ መሥራት ይሳነዋል፡፡ ሲሰጡት ደግሞ ኃጢአትን ተለማምዷልና ሌላ ፈቃድ በማምጣት ጠላት ሆኖ ይፈትነዋል፡፡ ‹‹ያዕቆብ በላ፣ ጠገበ፣ ወፈረ፣ ደነደነ፣ ሰባ፣ የፈጠረውንም እግዚአብሔርን ተወ፣ የመድኃኒቱንም አምላክ ናቀ፡፡ (ዘዳ 32፥15)
ሰውነት የሚፈልገውን ሁሉ እንደ ልቡ ካገኘና ያለ ገደብ የሚቀለብ ከሆነ ወደ ኃጢአት ለመገስገስ የተዘጋጀ መርከብ ነው፡፡ ሰውነት በተመቸውና ፈቃዱን ለመፈጸም ኃይል ባገኘ ጊዜ ነፍስ እየደከመች ትሄዳለች፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ሰውነት ፈጽሞ ከደከመና ከዛለ ሥራ መሥራት ያስቸግራል፡፡ ስለዚህ ሐዋርያው ‹‹ሰውነቴን እየጎሰምሁ አስገዛዋለሁ›› እንዳለ፡፡ በአግባቡ ሊያዝና ሊገራ ይገባዋል፡፡ (1ኛ ቆሮ 9፥27) በአጠቃላይ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ወንድሞች ሆይ ዕዳ አለብን እንደ ሥጋ ፈቃድ ግን እንኖር ዘንድ ለሥጋ አይደለም፡፡ እንደ ሥጋ ፈቃድ ብትኖሩ ትሞቱ ዘንድ አላችሁና፤ በመንፈስ ግን የሰውነትን ሥራ ብትገድሉ በሕይወት ትኖራላችሁ›› እንዳለ ከፈቃደ ሥጋ ጋር በመጋደል ፈቃደ ሥጋችንን ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛት ይገባናል፡፡
ለ. ከርኵሳን መናፍስት ጋር የሚደረግ ጦርነት ነው፡፡
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር እንጂ›› እንዳለ መንፈሳዊ ተጋድሎ ማለት ሰው ከሰው ጋር በመጣላት የሚያደርገው ትግል ሳይሆን ጥንተ ጠላታችን ከተባለው በእባብ ወይም በዘንዶ ከተመሰለው ዲያብሎስና ከእርሱ ጋር ካሉት ሠራዊቱና መልእክተኞቹ ጋር የሚደረግ ጦርነት ነው፡፡ (ኤፌ 6፥12)
ከአዳምና ከሔዋን ከልጃቸውም ከቃየን ጀምሮ ሰይጣን የሰው ልጆችን ዘወትር ይዋጋል፤ ከዘላለም የሞት ፍርድ ሥር ሊጥል ይሠራል፡፡ በዚህም ውጊያው ከነቢያት ፤ከሐዋርያት ፤ የእግዚአብሔር መንፈስ ካደረባቸው ሰዎች እንኳ ሳይቀር ብዙዎችን ጥሏል፡፡
ዛሬም በገዛ ባሕርያችን የሚገኘውን ፈቃደ ሥጋ በመጠቀም፣ የራሱን በመጨመርና የተለያዩ ፈተናዎችን በማቀናበር ይዋጋናል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹ባላጋራችሁ ዲያብሎስ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሣ አንበሳ ይዞራልና›› በዓለም ያሉት ወንድሞቻችሁ ያን መከራ በሙሉ እንዲቀበሉ እያወቃችሁ በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት፡፡›› እንዳለ ጠላት ዲያብሎስ ክርስቲያኖችን በኃጢአትና ሞት ሊውጥ ዘወትር ይተጋል፡፡ ማንም ሰው ደግሞ ከዚህ ፈተናና ውጊያ ሊያመልጥ አይችልም፤ ስለዚህ ሐዋርያት ‹‹በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት››፣ ‹‹የዲያብሎስን ሽንገላ ትቃወሙ ዘንድ እንዲቻላችሁ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ልበሱ፡፡›› እንዳሉን የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ለብሰን ልንዋጋው ይገባል፡፡ (1ኛ ጴጥ 5፥8-9፣ኤፌ 6፥11)
ሐ. የሚመጣውን ዓለም ደስታ ተስፋ እያደረጉ ብቻ በዚህ ዓለም ሕይወት ከደስታ ውጪ መሆን ማለት አይደለም፡፡
ደስታ በራሷ የቤተ ክርስቲያን መገለጫ የሆነች፤ ከእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የተሰጠች፤ ንጹሕ ፈርጥ ነች፡፡ (ገላ 5፥22)
እውነት ነው፤ በዚህ ዓለም ስንኖር መከራ አለብን፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስቀሉን ተሸክመን እንድንከተለው አዞናል፡፡ እያንዳንዱ ክርስቲያን በዚህ ምድር ላይ እስካለ ድረስ ከጨለማው ዓለም ገዢ ከዲያብሎስና ከሠራዊቱ የሚመጣ ልዩ ልዩ ፈተናና ከሥጋችንም ባሕርይ ከሚገኘው ክፉ ምኞትና ርኵሰት ሥራ እንዲሁም ከሌሎቹ የኃጢአትና የፈተና ዓይነቶች ጋር በማያቋርጥ እልህ አስጨራሽ በሆነ ትግል ውስጥ መኖሩ የግድ ነው፡፡ መከራና ስቃይ፣ ትግልና ጦርነት የሌለበት በዘለዓለማዊ ደስታ ብቻ የሚኖርበት ሕይወት በሚመጣው ዓለም የሚገኝ ነው፡፡
በዚህ ምድር በጉዞ ላይ ያለችው ቤተ ክርስቲያን ጉዞዋን ጨርሳ ድል ከነሱት አባላቷ ጋር አንድ እስክትሆን ድረስ መከራው፣ እንቅፋቱ፣ መሰደዱ፣ መራቡ፣ መጠማቱ የግድ ነው፡፡ ‹‹ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ ያስፈልገናል፡፡›› እንዲል (ሐዋ 14፥22)
ይህ ሲባል ግን በዚህ ዓለም የሚኖሩ ክርስቲያኖች ከደስታ የተራቆቱ ዘወትር በኅዘንና በስቃይ ብቻ የሚኖሩ ናቸው ማለት አይደለም፡፡ ክርስቲያኖች የሚለዩትና ዘወትር ለመለየት ጥረት የሚያደርጉት የውሸት ከሆነው ኃጢአት (ዝሙት፣ ርኩሰት፣ መዳራት፣ ጣዖትን ማምለክ፣ ምዋርት፣ ጥል፣ ክርክር፣ ቅንአት፣ ቁጣ፣ አድመኝነት፣ መለየት፣ መናፍቅነት፣ ምቀኝነት፣ መግደል፣ ስካር፣ ዘፋኝነት፣ ይህንም የሚመስል) ከሚገኘው ደስታ እንጂ ከእውነተኛውና ከሰማያዊው ደስታ አይደለም፡፡
መንፈሳዊ ተጋድሎ በመንፈስ ቅዱስ አነሳሽነትና ረድኤት መንፈስ ቅዱስ መሪና አስተማሪ፣ የሚያነቃቃና የሚያጽናና፣ የሚያርምና የሚገሥጽ፣ የሚረዳና የሚያጸና፣ በመሆን ስለ ክርስቶስ በክርስቶስ ጸጋ የሚከናወን በመሆኑ መከራንና ስቃይን በሚያስረሳ እውነተኛ ደስታና ሰላም የተሞላ ሕይወት ነው፡፡
ቅዱስ ጳውሎስና ቅዱስ ሲላስ ስለ ክርስቶስ በማስተማራቸው ምክንያት ገዢዎች ልብሳቸውን ገፈው በበትር እንዲመቱ አዘዙ በበትር ከመቷቸውም በኋላ በወኅኒ ቤት ጣሏቸው እነርሱ ግን ከጀርባቸው ደም እየፈሰሰ በመንፈቀ ሌሊት እንኳን እግዚአብሔርን በመዝሙር ያመሰግኑ ነበር፡፡ እውነተኛውና ሰማያዊው ደስታ በልቡናቸው ሞልቶ ነበርና፡፡ (ሐዋ 16፥22-25)
መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሐዋርያት እንዲህ ይለናል ‹‹ ሐዋርያትንም ወደ እነርሱ ጠርተው ገረፏቸው  በኢየሱስም ስም እንዳይናገሩ አዝዘው ፈቷቸው፡፡ እነርሱም ስለ ስሙ ይናቁ ዘንድ የተገባቸው ሆነው ስለተቆጠሩ ከሸንጎው ፊት ደስ እያላቸው ወጡ፡፡››(ሐዋ 5፥40-41)
ቅዱስ ዮሐንስ ካሲያን የተባለው አባት በተጋድሎ በግብጽ በረሃ ውስጥ ይኖሩ ስለነበሩት መነኰሳት ሲናገር ‹‹ እነዚህ ምድራዊ መላእክት ናቸው፤ የግብጽን በረሀዎች በደስታ ወደ ተሞላ መዝሙርና እግዚአብሔርን የማመስገኛ ገነትነት ለውጠዋልና››  ብሏል፡፡
በአጠቃላይ መንፈሳዊ ተጋድሎ ማለት ከተድላ ሥጋ፣ በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ በመሸሽ ሰማያዊና እውነተኘ በሆነ ሰላምና ደስታ ውስጥ መኖር ይህንንም ለማግኘት መጋደል ማለት ነው፡፡
2.    መንፈሳዊ ተጋድሎ ዓላማው ምንድነው?
ሀ. የድል አክሊል (የዘለዓለም ሕይወት) ለመቀበል
እግዚአብሔር አምላካችን ሰዎች ነፃ ፈቃዳቸውን ተጠቅመው ከአምላካቸው ጋር መኖር ከመረጡ ሊሰጣቸው ያዘጋጀው ከመነገርና ከመታሰብ በላይ የሆነ የዘለዓለም  ሕይወት አለ፡፡ የሰው ልጅ ሕሊናዊ ነፃ ፈቃዱ ደግሞ ከአዳምና ከሔዋን ውድቀት በኋላ በየጊዜው እየደከመና ወደ ኃጢአት እያዘነበለ መጥቷል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የሰው ልጅ በእግዚአብሔር ዘንድ ከብሮ ባየ ጊዜ ከአባቶቻችን ጀምሮ ዘወትር የሚቀና ክፉ ጠላትም (ዲያብሎስ) አለን፤ ባገኘው አጋጣሚ ስንፍናችንንና ድካማችንን እየተከተለ እነዚህንም በመጠቀም ዘወትር ከአምላካችን ሊለየን እንደሚተጋም ከላይ ተመልክተናል፡፡

ሽልማት፣ አክሊል የሚሰጠው ደግሞ ማሸነፍ ለሚችል ጎበዝ ሰው ነው፡፡ ሰነፍና ቸልተኛ ሰው ግን ሊሸለም አይገባውም አንድ ሰው ጎበዝ ወይም ሰነፍ መሆኑ የሚታወቀው ደግሞ በፊቱ ያጋጠመውን ውድድር ወይም ፈተናና መከራ ማሸነፍና ማለፍ ሲችል ብቻ ነው፡፡

ስለዚህ የመንፈሳዊ ተጋድሎ ዓላማ በገዛ ባሕርያችን ያለን መጥፎ የኃጢአት ዝንባሌና ጠላታችን ዲያብሎስ የሚያመጣብንን ፈተናና ሽንገላ ከእግዚአብሔር ርዳታና ቸርነት ጋር ሕሊናን በማንቃት፣ ራስን በመግዛትና ጠንክሮ በመጋደል አምላካችን ያዘጋጀልንን የድል አክሊል የዘላለም ሕይወትን መቀበል ነው፡፡ ‹‹ የተጠራህለትን የዘለዓለም ሕይወት ትቀበል ዘንድ መልካሙን የሃይማኖት ገድል ተጋደል›› አንዲል (1ኛ ጢሞ 6፥12) ሐዋርያቅ ቅዱስ ጳውሎስ ብዙ መከራዎችን አልፎ ገድሉን በድል አድራጊነት ሲፈጽም ‹‹ መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ፤ ሩጫዬን ጨርሻለሁ፤ ሃይማኖቴንም ጠብቄያለሁ፤ ወደ ፊት የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል፤ ይህም ጻድቅ ፈራጅ የሆነው ጌታ ያን ቀን ለእኔ ያስረክባል፤ ደግሞም መገለጡን ለሚወዱ ሁሉ እንጂ ለእኔ ብቻ አይደለም፡፡›› ብሏል ( 2ኛ ጢሞ 4፥7-8)
ለ. ለመንፈሳዊ እድገት
ክርስቲያናዊ ሕይወታችን ለፍሬ የሚበቃው የድል አክሊልን መቀዳጀት የምንችለው የማያቋርጥ (የማይቆም) መንፈሳዊ ዕድገት ሲኖረን ነው፡፡ በጥምቀት ያገኘነው አዲሱ ሕይወታችን ዘወትር ማደግ ይኖርበታል፡፡ ክርስቲያናዊ ሕይወታችን በዛፍ ተክል ይመሰላል፡፡ ከችግኝ ማፍላት ጀምሮ ፍሬ እስከሚያፈራለት ጊዜ ድረስ ያለው ድካም ቀላል አይደለም፡፡ የዛፉ ችግኝ እንዲያበቅል፣ እንዲለመልም፣ አንዲያብብና እንዲያፈራ አትክልተኛው ያልተቆጠበ ጥረት ማድረግ ይኖርበታል፤ በየጊዜው ውሃ ማጠጣት፣ ማረምና መኰትኰት፣ ፀረ ዕፅዋትና ፀረ ሕይወት የሆኑ በሽታዎችን መከላከል ያስፈልጋል፡፡ እንደዚሁ ክርስቲያናዊ ሕይወታችን አድጎ ለፍሬ እስኪበቃ ድረስ ዕለተ ዕለት ጠንክረን በትዕግሥት መሥራት በመንፈሳዊ ተጋድሎ መጽናት ይገባል፡፡ የመንፈሳዊ ተጋድሎም ዓላማው መንፈሳዊ ሕይወታችንን የሚያቀጭጩ  ከጸጋ እግዚአብሔርም የሚያራቁቱ ኃጢአትና የዲያብሎስ ፈተናን በመቃወም መንፈሳዊ ምግቦችንም በመመገብ አዲሱ ሕይወታችንን ማሳደግ ነው፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር 
Source: eotc-mkidusan.org

ዘመነ ጽጌ



ከገነት የተሰደደውን አዳምን ወደ ቀደመ ክብሩና መንበሩ ከዚያም ወደ ሚበልጥ ክብር ለመመለስ የተወለደው ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ገና ከህፃንንቱ ጀምሮ ስደትን እና መከራን ተቀብሏል፡፡


ጌታ ሲወለድ ሰብአ ሰገል «የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት አለ? በምሥራቅ ኮከቡን አይተን ልንስግድለት መጥተናል» እያሉ በኮከብ እየተመሩ በመጡ ጊዜ በይሁዳ፣ በገሊላና በሰማርያ የሮማውያን ተወካይ የነበረው ንጉሥ ሄሮድስ የጌታችን ንግሥና ምድራዊ ንግሥና መስሎት መንግስቴን ሊቀማኝ ነው ብሎ ደነገጠ፡፡ ፊሪሳውያን «መሲህ ተወልዶ ከሮማውያን አገዛዝ ነጻ ያወጣናል፡፡» ብለው ያምኑ እንደነበር ስለሚያውቅም ይህ የተፈጸመ መስሎት ጭንቀቱ በረታ፡፡ የተወለደውን ሕፃንም ለመግደል ተነሳ፡፡
ስለዚህም ሰብአ ሰገልን አስጠርቶ «ሂዱ ሕፃኑን ፈልጉ ፤ ባገኛችሁትም ጊዜ እኔም እንድሰግድለት ወደ እኔ ተመልሳችሁ ያለበትን ንገሩኝ» በማለት በሽንገላ ተናገራቸው፡፡


ጠቢባኑም ከሄሮድስ ከተለዩ በኋላ በኮከቡ እየተመሩ ጉዞአቸውን ቀጥለው ጌታችንን ከእናቱ ጋር አገኙት ፤ ተንበርክከው ሰገዱለት፤ ወርቅ ፣ ዕጣን፣ ከርቤ እጅ መንሻ አቀረቡለት፡፡


የእግዚአብሔር መልአክ ወደ ሄሮድስ እንዳይመለሱ፤ ነገር ግን መንገድ ቀይረው ወደ ሀገራቸው እንዲሄዱ በነገራቸው መሠረት በሌላ መንገድ ወደ መጡበት ተደብቀው ተመለሱ፡፡


«እነርሱም ከሄዱ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በሕልም ለዮሴፍ ታይቶ «ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነስ፤ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ግብጽ ሽሸ፤ እስክነግርህም በዚያ ተቀመጥ አለው፡፡ » /ማቴ. 2 13  14/


ዮሴፍም ተነሣ፤ በዕድሜዋ በጣም ልጅ የነበረችው እመቤታችን ገና የተወለደውን ሕፃን አቅፋ የምትቀመጥበት አህያም ተዘጋጀ፡፡ ጉዞአቸውን ጀመሩ፡፡ ከእስራኤል ወደ ግብጽ በእግር ለመሔድ የሲናን በረሃ ማለፍ የግድ ነው፡፡ በዚያን ዘመን ከእስራኤል ወደ ግብጽ የሚወስዱ ሦስት የተለያዩ መንገዶች ነበሩ፡፡ በሽፍቶች ላለመጠቃት መንገደኞች በቡድን በቡድን ሆነው በእነዚህ መንገዶች ይሔዱ ነበር፡፡


እነርሱ ግን ንጉሥ ሔሮድስ ተከታትሎ ሊይዛቸው ስለሚችል በእነዚህ መንገዶች መሔድ እንደሌለባቸው ግልጽ ነው፡፡ ስለዚህም በእግዚአብሔር መልአክ እየተመሩ ባልታወቁ መንገዶች መሔድ ነበረባቸው፡፡ ለበርካታ ቀናትና ሳምንታት ሸለቆዎችን በመውረድና ኮረብታዎችን እየወጡ ጉዛአቸውን ቀጠሉ፡፡ ሽማግሌው አናጢ ዮሴፍ ከፊት ሁኖ አህያዋን ባልተስተካከለውና ማለቂያ የሌለው በሚመስለው የበረሃ መንገድ ላይ ይመራ ነበር። ሰሎሜም ስንቃቸውን ይዛ ከኋላ ትከተል ነበር፡፡ በጣም አስቸጋሪ እና አስጨናቂ ጉዞ ነበር፡፡ ቀን ቀን የሚያቃጥለውን የፀሐይ ሐሩር ሌሊት ሌሊት ደግሞ የበረሀውን ውርጭ /ብርድ/ መታገል ነበረባቸው ምግባቸውንም በተአምራት ያገኙ ነበር፡፡


በመጨረሻም በመጽሐፈ ስንክሳር እንደተመዘገበው ግንቦት 24 ቀን ግብጽ ደረሱ፡፡ በግብጽም ባሉ የተለያዩ ከተሞች ተዘዋወሩ፣ ጌታም በተለያዩ ቦታዎች በርካታ ተአምራትን አደረገ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ተቀብለው ሲያስተናግዷቸው ሌሎች ደግሞ አሳደዋቸዋል፤ መከራንም አጽንተውባቸዋል፡፡ በዚሁ ስድታቸው ወቅት ጌታ እና እመቤታችን ወደ ኢትዮጵያም መጥው ሀገራችንን ባርከዋል።


ለሦስት ዓመት ተኩል ያህል በስደት ከቆዩ በኋላ ሄሮድስ ሞተ። ሄሮድስም ከሞተ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በግብጽ ለዮሴፍ በሕልም ታይቶ «የሕፃኑን ነፍስ የፈለጉት ሞተዋልና ተነሣ፤ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ አለው፡፡ እርሱም ተነስቶ ሕጻኑንና እናቱን ይዞ ወደ እስራኤል ሀገር ገባ» ማቴ 2-19-21/


ቅዱስ ዮሴፍ ይህንን «.. ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ..» የሚለውን የመልአኩን ቃል የሰማው ቁስቋም በምትባል በግብጽ ባለች ቦታ ነው፡፡


በኋላ በዚህች ቦታ ላይ የእመቤታችን ቤተክርስቲያን ተሰርቶ ቅዳሴ ቤቱ ኅዳር 6 ቀን  ከብሯል። ሃያ ሦስተኛው የእስክንድርያ ፓትርያርክ ቴዎፈሎስ /384-412 ዓ.ም/ ደግሞ በጌታ እና በእመቤታችን ስደት ወቅት የሆነውን ነገር እንዲገለጥለት ለብዙ ጊዜ ጸሎት ካደረገ በኋላ ህዳር 6 ቀን እመቤታችን ተገልጣለት በጉዞው ወቅት የሆነውን ነገር ሁሉ ነግራዋለች፡፡ ስለዚህ ኅዳር 6 ቀን በሁሉም ምሥራቃውያን አብያተ ክርስቲያናት የእመቤታችን ከስደት የመመለሷ ነገር የሚታሰብበት ሁኗል፡፡


በሀገራችን መስከረም 25 ቀን ዘመነ ክረምት አልፎ መስከረም 26 ቀን ዘመነ ጽጌ ይጀምራል፡፡ ጽጌ ማለት አበባ ማለት ሲሆን ዘመነ ጽጌ ማለት የአበባ ዘመን ማለት ነው፡፡ ዘመኑ አበቦች የሚያብቡበትና ሜዳዎችንና ተራሮችን የሚያስጌጡበት ዘመን ነው፡፡ ፍሬ የተባለ ጌታን ያስገኘች እመቤታችን በአበባ ትመሰላለችና ዘመኑ የጌታንና የእመቤታችንን ነገር በአበባና በፍሬ ለመመሰል የተመቸ ነው፡፡


ስለዚህም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከመስከረም 26 ቀን ጀምሮ እስከ ኅዳር 6 ቀን ድረስ የጌታን እና የእመቤታችን ስደት ታስባለች፡፡


በዚህ ዘመን ቅዱስ ያሬድ እና አባ ጽጌ ድንግል ባዘጋጇቸው ድርሰቶች የጌታችን እና የእመቤታችን ስደት በማኅሌት ይታሰባል፤ ምስጋና እና ልመና ይቀርባል። እነዚህን ለየሳምንቱ በሚዘጋጁት ትምህርቶች እናቀርባቸዋለን፡፡


ከዚህም በተጨማሪ ስደቱን ለማሰብና በረከት ለማገኘት በርካታ ክርስቲያኖች ዘመኑን በጾም ያሳልፉታል፡፡


ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በማቴዎስ ወንጌል ትርጓሜው /Homilies on the Gospel of Saint Mathew/ ይህንን ስደት አስመልክቶ ያስተማረውን ትምህርት ከዚህ ቀጥለን አቅርበናል፡፡


ሰብአ ሰገልም ከሄዱ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በህልም ለዮሴፍ ተገልጾ፡- ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነሳና ሕፃኑን ከእናቱ ይዘህ ወደ ግብፅ ሽሽ እስክነግርህም ድረስ በዚህ ተቀመጥ አለው እርሱም  ተነስቶ  ሕፃኑና እናቱን ያዘና ከጌታ ዘንድ በነቢይ ልጄን  ከግብፅ ጠራሁት የተባለው ይፈጸም ዘንድ ወደ ግብፅ ሄደ። ሄሮድስም እስኪሞት ድረስ በዚያ ኖረ።


ከዚህ በኋላ ሄሮድስ ሰብአ ሰገል እንደተሳለቁበት ባወቀ ጊዜ እጅግ ተቆጥቶ /ጌታን ለማስገደል በማሰብ / ጌታ በተወለደባት ከተማ በቤተልሔምና በአውራጃዋ የነበሩትን ሕጻናትን አስገደለ፡፡ /ማቴ. 1.13-18/


እዚህ ላይ ሕፃኑን በተመለከተና ሰብአ ሰገልን በተመለከተ ልንጠይቃቸው የሚገቡ ነገሮች አሉ፡፡ ለምን ሰብአ ሰገልም፣ ሕፃኑም /ጌታም/ በዚያው አልቆዩም? ለምን እነርሱ እንደ ተሳዳጅ /fugitive/ በድብቅ ወደ ፋርስ፣ እርሱም ከእናቱ ጋር ወደ ግብፅ ሄዱ?


ከዚህ ሌላ ምን መደረግ ነበረበት? ጌታ በሄሮድስ እጅ መውደቅና ከዚያ አለመገደል ነበረበት? እንዲህ ቢያደርግም ኖሮ ሥጋን መዋሃዱ ግልጽ አይሆንም ነበር፡፡ የክርስቶስ የማዳን ሥራም አይታመንም ነበር፡፡


ሥጋን መዋሃዱን የሚያሳዩ ይህን የመሳሰሉ በርካታ ነገሮች ተደርገው፣ ሥጋን ለበሰ /ተዋሃደ/ መባሉ ተረት /ውሸት/ ነው የሚሉ ካሉ ሁሉን ነገር እንደ አምላክነቱ ብቻ ቢያደርገውማ ከእነዚህ የሚበልጡ ብዙዎች በተሳሳቱ ነበር፡፡


ሰብአ ሰገልንም በፍጥነት የላካቸው አንደኛ ለፋርስ ሰዎች መምሀራን እንዲሆኑ ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ጌታን ለማስገደል ላሰበው ሄሮድስ እየሞከረ ያለው የማይቻል ነገርን መሆኑን አስረድቶ የሄሮድስን እብደት ለማቆምና ንዴቱን አስታግሶ ከከንቱ ድካሙ እንዲያርፍ ለማድረግ ነበር፡፡


ምክንያቱም አምላካችን ጠላቶቹን በግልጽ እና በኃይል ማስገዛት ብቻ ሳይሆን በቀላል እና ትንሽ በሚመስሉ ነገሮች ማሳመንም፣ ያውቅበታል፡፡


ለምሳሌ ግብጻውያንን በግልጽ /በኃይል/ ንብረታቸውን ለእስራኤል እንዲያስረክቡ ማድረግ ሲችል እርሱ ግን በጥበብ ያለ ጦርነት ይህንን እንዲያደርጉ አድርጎአቸል፡፡ ይህም አድራጎቱ ከሌሎቹ ተአምራት ባልተናነሰ ሁኔታ በጠላቶቹ ዘንድ የሚፈራ አድርጎታል፡፡


ለምሳሌ ፍልስጤማውያን ታቦተ ጽዮንን ማርከው በመውሰዳቸው በተቀጠቀጡ ጊዜ የሀገራቸውን ጠቢባን ከእግዚአብሔር ጋር ለመዋጋት እንዳይሞክሩ በነገሯቸው ጊዜ ከሌሎች ተአምራት ጋር ይህንን እግዚአብሔር በሥውር የሠራውንም ሥራ አንስተውታል፡፡ በግልጽ ከተደረጉት የተለየ አድርገው አላዩትም፡፡ 1ኛ ሳሙ. 6-6


በዚህ ጊዜም የተደረገው ከዚህ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ደም የጠማውን ነፍሰ ገዳይ ሊያስደንቅ የሚችል ነገር ነበር፡፡ ሄሮድስ ሊያስብ የሚገባው እንዲህ ነበር፡፡ ሰብአ ሰገል እንደካዱት፣ እንደተናቀና መሳቂያ መሳለቂያ እንደሆነ ባወቀ ጊዜ መደንገጥ ትንፋሹ መቆም ነበረበት፡፡ እነዚህ ሁሉ ነገሮች ካላሻሉት /ካላስተካከሉት/ ግን እርሱን ከጥፋቱ ለመመለስ እነዚህን ሁሉ ነገሮች ያደረገ እግዚአብሔር በእርሱ ጥፋት ሊጠየቅ አይችልም፡፡ ሄሮድስ ከዚህ በኋላ የሆኑትን ነገሮች ሁሉ ያደረገው የእብደቱ ብዛት እነዚህ ሁሉ እውነተኛ ግልጽ ነገሮች እንዲያሳምኑት ስላላደረገ ነው፡፡ ስለዚህ ከጥፋቱ መመለስ አልቻለም፡፡ በክፋቱ ስለ ቀጠለበትም ስለ ሞኝነቱ የከፋ ቅጣት ተቀብሏል፡፡


ሕፃኑ ለምን ወደ ግብጽ ሄደ? የመጀመሪያውን ምክንያት ወንጌላዊው ራሱ በግልጽ ይነግረናል፤ «ልጄን ከግብጽ ጠራሁት የተባለው እንዲፈጸም ወደ ግብጽ ሄደ» /ማቴ. 1-15/


ከዚህም በተጨማሪ በዚህ ድርጊት ለዓለም መልካም ተስፋ ተሰብኳል፡፡ በዚያን ጊዜ በዓለም ካለው ቦታ ሁሉ በከፋ ሁኔታ ባቢሎን /ፋርስ/ እና ግብጽ በእምነተ ቢስነት /በአምላክ አልባነት/ ነበልባል ተቃጥለው ነበር፡፡ እርሱም ከመጀመሪያው ሁለቱንም እንደሚያስተካክል ምልክት ሰጥቶ ሰዎችን ማዳኑ /ስጦታዎቹ/ ለዓለሙ በሙሉ እንደሆኑ አውቀው በተስፋ እንዲጠብቁ አደረጋቸው፡፡ ለዚህም ወደ አንዱ /ባቢሎን፣ ፋርስ/ ሰብአ ሰገልን ላከ፣ ሌላውን /ግብጽን/ ራሱ ከእናቱ ጋር ጎበኘ፡፡


ከዚህም ሌላ በዚህ የምንማረው ሌላ ትምህርት አለ፤ ከፍ ያለ ጽናት ሊኖረን እንደሚገባ፡፡ ይህ ምን ዓይነት ነው? ክፉ ሃሳብ /ተንኮል/ እና ክፉ ድርጊት ገና በመጠቅለያ ካለበት ጊዜ ጀምሮ በእርሱ ላይ እንደሆነ ተመልከቱ፡፡ በልደቱ ጊዜ መጀመሪያ ክፉ ነፍሰ ገዳይ፣ ተነሳበት ከዚያም ስደት እና ሀገርን ትቶ መሄድ ተከተለ፡፡ ያለ ምንም ጥፋትና በደል ከቤቷ እንኳን ርቃ ተጉዛ የማታውቀው እናቱ ወደ አረመኔዎች /barbarians/ ሃገር ተሰደደች፡፡ አስጨናቂና አስቸጋሪ የሆነ ረጅም ጉዞ እንድታደርግ ታዘዘች፡፡ ይህንን የሰማ ሰው መንፈሳዊ አገልግሎት ሲፈጽም አስጨናቂ ችግሮችና ህመሞች ቢደርሱበትና ህመሞች ቢያጋጥሙት መሸበር የለበትም፡፡


«የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ ስለፈጸምኩ መሸለም መከበርና ታዋቂ መሆን ሲገባኝ ለምን ይህ ሆነ?» ማለትም የለበትም፤ ነገር ግን ሁላችንም ይህንን እንደ ምሳሌ ወስደን ሁሉን ነገር በደስታ መቀበል አለብን፡፡ መንፈሳዊ ነገሮች ባሉበት ሁሉ ተቃዋሚ እንደማይጠፋ እና የመንፈሳዊ ነገሮች ሂደትም ይህ መሆኑንም መረዳት አለብን፡፡


ቢያንስ ይህ ነገር የሆነው በሕፃኑና በእናቱ ብቻ ላይ ሳይሆን በሰብአ ሰገልም ላይ መሆኑን እናስተውል፡፡ እነርሱም እንደ ተሳዳጅ /fugitive/ ሆነው በምስጢር እንዲሸሹ ሆነዋል፡፡


ሌላም አስደናቂ ነገር ተመልከቱ፡፡ የእግዚአብሔር ሐገር፣ የተስፋ ምድር የተባለችው ፍልስጤም በጌታ ላይ የተንኮል መረብ /ሤራ/ ስትዘረጋ የኀጢአትና የጣኦት አምልኮ ሀገር የሆነችው ግብጽ ደግሞ ተቀብላ አዳነችው፡፡


ጌታችን በእግረ ሥጋ በተመላለሰባቸው ዘመናት ያደረጋቸው አብዛኞቹ  ነገሮች ወደፊት ሊመጡ ላላቸው ነገሮች ትንቢት ናቸው፡፡


ዮሴፍ ጌታንና እናቱን ይዞ ወደ ግብጽ እንዲሄድ በመልአክ ታዘዘ፡፡ ግብጽ በሥፋት ጣኦት የሚመለክባት ሀገር ነበረች፡፡ ይህም በኋላ ክርስትና በአምልኮት ባዕድ ወደ ነበሩ ህዝቦች /አሕዛብ/ ዘንድ ለመውሰዷ ትንቢት /ምልክት/ነው፡፡ እመቤታችን ጌታን ይዛ ወደማታውቀው ሀገር ስትሰደድ ቤተልሄም /ይሁዳ/ ሄሮድስ ባስገደላቸው ሕፃናት በሰማዕታት ደም ተጥለቅልቃለች፤ የሄሮድስ ጭፍጨፋና ሕፃናቱን መግደሉ ወደፊት ክርስቲያኖች በአይሁድ እጅ ለሚቀበሉት ሰማዕትነት ምሳሌ ነው፡፡


መልአኩ ተገልጦ የተነጋገረው ከእመቤታችን ጋር ሳይሆን ከዮሴፍ ጋር ነበር፡፡ ምን አለው? «ተነሳ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ..» የእመቤታችን በግብረ መንፈስ ቅዱስ መጽነስ ሲነግረው ያለው «እጮኛህን ማርያምን ለመውሰድ አትፍራ» ነበር፡፡ አሁን ግን እጮኛህን አላለውም «የሕፃኑን እናት» አለው እንጂ፡፡ ምክንያቱም እመቤታችን ጌታችንን ከወለደች እና በጌታ ልደት ጊዜ የሆኑትን ነገሮች /ኮከቡን፣ ሰብአ ሰገልን/ ካየ በኋላ ሁሉን ነገር ተረድቶ ተረጋግጦ ነበር፡፡ በቂ ነገር ዓይቶ፣ ባየው ነገር ተረጋግቶ ነበር፡፡ ስለዚህ መልአኩ አሁን በግልጽ ይናገራል «ልጅህን» ወይም «እጮኛህን» አላለም፡፡ «ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ግብጽ ሂድ አለው» እንጂ፡፡ የስደቱንም ምክንያት አብሮ ይነግረዋል፤ «ሄርድስ የሕፃኑን ነፍስ ይፈልጋልና፡፡»


ዮሴፍ ይህንን ሲሰማ ቅር አልተሰኘም፤ «ይህን ነገር ለመረዳት ይከብዳል፤ ሕዝቦቹን ያድናቸዋል አላለከኝም ነበር? አሁን ደግሞ ራሱን እንኳን ማዳን አይችልምን? እኛም ከቤታችን ወጥተን ርቀን ለብዙ ጊዜ መሰደድ አለብን አሁን ያለት ነገሮች ከተሰጠው ተስፋ /ቃል/ ጋር ተቃራኒ ናቸው፡፡» አላለም ጻድቅ እና እውነተኛ አማኝ ነበርና፡፡


ምንም እንኳን መልአኩ መመለሻውን ግልጽ ሳያደርግ እስከምነግርህ ድረስ በዚያው ተቀመጥ ቢለውም ስለሚመለሱበት ጊዜ አልተጨነቀም፤ አልጠየቀምም፡፡ ዮሴፍ ፍርሃትም እንኳን አላሳየም፡፡ ሁሉንም ነገር በደሰታ ተቀበለ እንጂ፡፡


ሰውን ወዳጅ የሆነው እግዚአብሔር መከራንና ደስታን በሰዎች ሕይወት ላይ ያመጣል፡፡ በችግር ወይም በደስታ ብቻ አያኖርም፡፡ ነገር ግን ሁለቱንም ችግርን /ሀዘንን/ እና ደስታን /ሃሴትን/ እያፈራረቀ ያመጣል፡፡ አሁንም ያደረገው ይህንኑ ነገር ነው፡፡ ዮሴፍ ድንግልን ጸንሳ ባያት ጊዜ ተጨነቀ፤ ተረበሸ፤ ታወከ፡፡ በዚህ መሃል ግን መልአኩ ተገልጦ ፍርሃቱን አስወገደለት፡፡ ሕፃኑን ተወልዶ ባየ ጊዜም ከፍ ያለ ደስታ ተደሰተ፡፡ ደስታው ብዙም ሳይቆይ አደጋ መጣ፤ በሰብአ ሰገል መምጣት ከተማው ተረበሸ ንጉሡም ከእብደቱና ከክፋቱ የተነሳ የተወለደውን ሕፃን ሊገድል ተነሳ፡፡ ይህ ጭንቀት ደግሞ በደስታ ተተካ ኮከቡና የሰብአ ሰገል ለጌታ መስገድ እጅግ አስደሳች ነበሩ፡፡ ከዚህ ደስታ በኋላም ጭንቀትና ፍርሃት መጣ፡፡ መልአኩ «ንጉሥ ሄሮድስ የሕፃኑን ነፍስ ይፈልጋል፡፡» ብሎ ነገረው፡፡


በዚህ ጊዜ ጌታችን በሕዝብ ፊት ተዓምራት ለማድረግ ጊዜው ገና ነውና መሰደድ አስፈለገው፡፡ ምክንያቱም ገና በልጅነቱ ተአምራትን በአደባባይ /በሕዝብ ፊት/ ቢያደረግ፣ ሥጋን እንደተወሃደ አይታመንም ነበር፡፡


በአንድ ጊዜ ሁሉን ማድረግ ሲችል ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማኅጸን ያደረው፣ እንደ ሕፃናት ጡትን እየጠባ፣ በጥቂት በጥቂቱ ያደገው፣ ሥራውን እስኪጀምርም ሠላውን ዘመን በዝምታ /በስውር ተዓምራት/ ያሳለፈው፡- የተዋህዶን ነገር እንረዳ ዘንድ ነው፡፡


አይሁድ ትንቢቱን በተመለከተ ጥያቄ ቢያነሱ እና ልጄን ከግብጽ ጠራሁት የተባለው ስለ እኛ ነው ቢሉን ይህ የትንቢት አካሄድ /መንገድ/ ነው እንላቸዋለን፡፡ ብዙ ጊዜ ስለተወሰኑ ሰዎች የተናገረው የሚፈጸመው በሌሎች ነው፡፡ ያዕቆብ ሊሞት ሲል ልጆችን ሰብስቦ በኋለኛው ዘመን ምን እንደሚደርስባቸው ሲነገራቸው እንዲህ ብሎ ነበር፡-


ስምኦንና ሌዊ ወንድማማች ናቸው፤


ሰይፎቻቸው የአመጽ መሣሪያ ናቸው፡፡


ከምክራቸው ነፍሴ አትግባ፡፡


ከጉባኤያቸውም ጋር ክብሬ አትተባበር


በቁጣቸው ሰውን ገድለዋልና


በገዛ ፈቃዳቸው በሬን አስነክሰዋልና፡፡


በያዕቆብ እከፍላቸዋለሁ፡፡ በእስራኤልም እበትናቸዋለሁ፡፡ ዘፍ. 49-7


ይህ ግን በእነርሱ አልተደረገም በልጆቻቸው እንጂ፡፡ በዘፍ. 9-25 ላይ ተጽፎ እንደሚገኘውም ኖህ እንዲህ ብሎ ነበር፡- «ከነአን ርጉም ይሁን ለወንድሞቹም የባሪያዎች ባሪያ ይሁን» ይህ የተፈጸመው በከንአን ሳይሆን በእርሱ ዘሮች ነው፡፡


ይህ መቼ እና እንዴት እንደሆነ በመጽሐፈ ኢያሱ እና በመጽሐፈ ዜና መዋዕል፤ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ እንዲህም ሆነ በዮርዳኖስ ማዶ በተራራማው በቆላውም በታላቁ ባሕር ዳርና ሊባኖስ ፊት ለፊት የነበሩ ነገሥታት ሁሉ ኬጢያዊ፣ አሞራዊም፣ ከነአናዊም፣ ኢያቡሳዊም፣ ይህን በሰሙ ጊዜ ኢያሱንና እስራኤልን ሊወጉ ወጡ፡፡


በዚያም ቀን ኢያሱ ለማኅበሩ በመረጠው ሥፍራ እስከ ዛሬ ድረስ፣ ለእግዚአብሔር መሠዊያ እንጨት ቆራጮች ውኃም ቀጂዎች አደረጋቸው፡፡ /ኢያ. 9-1-27/


1ኛ ዜና.8-7 ሰሎሞንም ኬጤያውያንንም፣ አምራውያንንም፣ ፌርዜያውያንንም ኢያቡሳውያንንም የቀሩትን ከእስራኤል ወገን ያልሆኑትን ሕዝብ ሁሉ... ገባሮች አድርጎ መለመላቸው፡፡


ይስሐቅ «ለወንድሞችህ ጌታ ሁን፡፡ የእናትህም ልጆች ይስገዱልህ»፡፡ ብሎ ያዕቆብን የመረቀው ምርቃት የተፈፀመው በእርሱ ሳይሆን በልጆቹ ነው፡፡ ዘፍ. 27-19


ስለዚህ እርሱ ባይወለድ ኖሮ፣ ትንቢቱ ፍጻሜውን አያገኝም ነበር፡፡ ወንጌላዊውም ያለውን አስተውሉ፡- «ይፈፀም ዘንድ፡፡» ይህም እርሱ ባይመጣ አይፈፀምም ነበር ማለት ነው፡፡


በዚህኛውም ጊዜ የተደረገው /የሆነው/ ከዚህ ጋር ተመሳሳይ የሆነ ነገር ነው፡፡ መጀመሪያ ለእስራኤል የተነገረው ነገር በኋላ በጌታ ተፈጽሟል፡፡ ደግሞስ የእግዚአብሔር እውነተኛ ልጅ ሊባል የሚችለው የትኛው ነው? ጥጃን ያመለከና ለቤልሆር ልጆቹን የሰዋ? ወይስ በባሕሪው ልጅ የሆነና የወለደው አባቱ «የምወደው ልጄ» ብሎ የሚያመሰግነው?


ከዚህም ሌላ /ግብጽ መሄዳቸው/ እመቤታችን ከፍ ያለ ክብር ያላት እንደሆነች እንዲታወቅ ተደርጓል፡፡ ህዝቡ የሚመኩበትን ከእግዚአብሔር ያገኙትን ስጦታ እርሷም ለራሷ አግኝታለችና፡፡ ማለትም፣ እነርሱ ከግብጽ በመውጣታቸው /ከስደት በመመለሳቸው/ ይመኩና ይኮሩ ነበር፡፡ ይህንኑ የሚመኩበትን ነገር ለእመቤታችንም ስጣት፡፡


ያዕቆብና ህዝበ እስራኤል ወደ ግብጽ በመሄዳቸውና ከዚያም በመመለሳቸው የእርሱን ግብጽ ሄዶ መመለስ ምሳሌ እየፈጸሙ ነበር፡፡ እነርሱ ግብጽ የሄዱት በረሃብ /በድርቅ/ የመጣ መሞትን ለማምለጥ ነበር፡፡ እርሱ ደግሞ በተንኮል መሞትን ለማምለጥ ነው፡፡


እነሱ /ህዝበ እስራኤል/ ግብጽ መሄዳቸው ከረሃቡ /ከድርቁ/ ተርፈዋል፡፡ እርሱ ግን እዚያ በመሄዱ በኪዳተ እግሩ /በእግሩ በመርገጥ/ ምድሪቱን ቀድሷታል፡፡


በዚህ ራሱን ዝቅ በማድረጉ መሀልም ግን የአምላክነቱ ማሳያዎች /ምልክቶች/ ተገልጸዋል፡፡ ሰብአ ሰገልና እርሱን ለማምለክ በኮከብ እየተመሩ መጡ፤ አውግስጦስ ቄሳርም የሕዝብ ቆጠራ አዋጅ በማወጅ ልደቱ ቤተልሔም እንዲሆን አገለገለ፤ በግብጽም በርካታ ተዓምራት ተደርገዋል፡፡


አሁን ወደ ግብጽ ብንሄድ በረሃው ከማንኛውም የአትክልት ስፍራ የተሻለ ሥፍራ ያማረ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በመላእክት አምሳል ያመሰግኑበታል የሰማእታት ብሔር፣ የደናግል በአት፣ የሰይጣን አገዛዝ ድል የተመታበትና የክርስቶስ መንግስት ደምቆ የሚያበራበት ቦታ ነው፡፡


በትምህርተ ሃይማኖታቸው /doctrine/ ካላቸው ትክክለኛነት በተጨማሪ፣ በህይወታቸውም ያላቸውን ቁርጠኝነት ያሳያሉ፡፡ ያላቸውን ሁሉ ትተው ራሳቸውን ከዓለም ካገለሉና ለዓለሙ በሙሉ ከተሰቀሉ በኋላ በድጋሚ የተቸገሩትን ይረዱ ዘንድ የጉልበት ሥራ ይሠራሉ፡፡


ስለሚጾሙና ብዙ ጊዜ በተመስጦ ስለሚያሳልፉ፤ ቀናቱን /ጊዜን/ ሥራ በመፍታት /ቦዝነው/ ማሳለፍ ተገቢ ነው ብለው አያስቡም፡፡ ስለዚህም ቀኑን በጸሎት ሌሊቱንም በዝማሬና በትጋት ያሳልፉታል፡፡ ከዚህም የሐዋርያውን አሰር ይከተላሉ፡፡


«ከማንም ብር ወይም ወርቅ አላስፈለገኝም እነዚህ እጆቼ በሚያስፈልገኝ ነገር ለእኔና ከእኔ ጋር ላሉት እንዳገለገሉ እናንተ ታውቃላችሁ፡፡ እንዲህ እየደከማችሁ ድውያንን ልትረዱና፣ «እርሱ ራሱ ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብጽዕ ነው» የሚለው የጌታን የኢየሱስን ቃል ልታስቡ ይገባችሁ ዘንድ አሳየኋችሁ፤» ሐዋ. 10-34 ይህንን የሐዋርያውን ቃል ሲሰሙ በበረሃ ያሉት የግብጽ መነኮሳት እንዲህ ይላሉ፡- «እርሱ /ሐዋርያው/ በእግዚአብሔር ቃል እንዲመግባቸው ብዙዎች እየጠበቁት የእጅ ሥራ ይሠራ ከነበረ፣ መኖሪያችንን በገዳም፣ በዱር፣ በበረሃ ያደረግን፣ የከተማ ጾር /ፈተና/ የቀረልን እኛማ ከጸሎታችንና ከተመስጦአችን የተረፈንን ጊዜ ለተመሳሳይ ሥራ ልናውለው ምን ያህል ይገባናል)!»


እኛም ራሳችንን እንመርምር ሀብታምም ድሃም የሆንን እነዚህ መነኮሳት ከሰውነት /እጅና፣ እግር/ በስተቀር ምንም የሌላቸው ሲሆኑ የተቸገሩትን ለመርዳት እንዲህ ከወጡና ከወረዱ የተረፈንን እንኳን ለእነዚህ ሰዎች /ችግረኞች፣ ድውያን/ የማንሰጥ እኛ ለዚህ አድራጎታችን ምን ምክንያት፣ ምን ማስተባበያ ማቅረብ እንችላለን፡፡


ታላቁን አባት ቅዱስ እንጦንስን እናስታውስ፡፡ ይህ ሰው የተወለደው ፈርኦን በተወለደበት ሀገር ነው፡፡ ነገር ግን በዚህ ምክንያት እነርሱን አልመሰለም፡፡ የነበረው ሰማያዊ ራእይ ስለጠበቀው እግዚአብሔር በሚወደው መልኩ ህይወቱን አሳልፏል፡፡ ከጽድቁ የተነሳ ከእርሱ በኋላ የሚመጡ መነኮሳት ምን ዓይነት እንደሚሆኑ እግዚአብሔር አሳይቶታል፡፡


ጻድቁ እንጦንስን ታሪክ ማንበብና ማድነቅ ብቻ ሳይሆን በሕይወት መተርጎምም ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን አለመበርታት ቦታን፣ አለመማርን፣ የአባቶችን መርገም... ምክንያት አናድርግ፡፡


ነገሮችን በማስተዋል ስንመለከት እነዚህ ሁሉ ነገሮች ለእኛ መሰናክል መሆን አይችሉም፡፡ አብርሃም ጣኦት አምላኪ አባት ነበረው /ኢያ. 24-2/ ነገር ግን የአባቱን ክፋት አልወረሰም፣ የሕዝቅኤልም አባት አካዝ ኀጢአተኛ ሰው ነበር፡፡ ሕዝቅያስ ግን የእግዚአብሔር ወዳጅ ነበር፡፡


ዮሴፍም በግብጽ ሆኖ ራሱን በትምህርት አስጊጧል፡፡ ሦስቱ ሕፃናትም በባቢሎን ቤተመንግስት ሆነው ታላቅ ራስን መግዛት አሳይተውናል፡፡ ሙሴም በግብጽ ነበር፣ ቅዱስ ጳውሎስም በዓለም ነበር፤ ነገር ግን እነዚህን ሁሉ ያሉበት ቦታና ሁኔታ ከጽድቅ ጉዞአቸው አላደናቀፋቸውም፡፡


ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን

Source: http://eotc-mkidusan.org