13

.

"በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው::" የማቴዎስ ወንጌል 7: 4

"እናንተ የተጠማችሁ ሁሉ፥ ወደ ውኃ ኑ፥ ገንዘብም የሌላችሁኑና ግዙ ብሉም ኑ ያለ ገንዘብም ያለ ዋጋም የወይን ጠጅናወተት ግዙ።" ትንቢተ ኢሳይያስ 55 : 1

Wednesday, September 14, 2011

የራሔል እንባ

የራሔል እንባ

        መልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው

« እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ የኀዘን የልቅሶና የጩኸት ድምጽ በራማ ተሰማ ፤ ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች ፤ የሉምና ስለ ልጆችዋ መጽናናትን እንቢ አለች። እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ድምጽሽን ከለቅሶ ዐይኖችሽንም ከእንባ ከልክዩ ፤ ለሥራሽ ፤ ዋጋ ይሆናልና ፥ ይላል፡፡ እግዚአብሔር ፤ ከጠላትም ምድር ይመለሳሉ። ለፍጻሜሽም ተስፋ አለ ፥ ይላል እግዚአብሔር ፥ ልጆችሽም ወደ ሀገራቸዎ ይመለሳሉ። » ኤር ፴፮ ፥፲፭ ፡፡
          ቅዱሳን ነቢያት የሚናገሩት ስለ ዘመናቸው ብቻ አይደለም ፤ ከዘመናቸው ጋር በማገናዘብ ስላለፈው ይናገራሉ ፥ ስለሚመጣውም ይተነብያሉ። ዓረፍተ ዘመን ሳይገታቸው ኃላፊያትንም መጻእያትንም ይተረጉማሉ። በመሆኑም ይህ ቃለ ኤርምያስ  ወደኋላም ወደፊትም የሚሠራ ነው። ለጊዜው እስራኤል ዘሥጋ በግብጽ የባርነት ዘመን የነበሩበትን ዘመን ያስታውሳል ፥ ለፍጻሜው ደግሞ በዘመነ ሥጋዌ መባቻ ማለትም መድኅነ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደ ጊዜ የተፈጸመውን ያሳያል።
      እስራኤል በባዕድ ሀገር በግብፅ በዮሴፍ ስም ተወደው ተከብረው ይኖሩ ነበር፡፡ በኋላ ግን ዮሴፍን የማያውቅ ፥ አንድም ደግነቱን ጥበቡን የማያውቅለት ንጉሥ ተነሥቶ ቀንበር አጠበቀባቸው። ይኸውም፦ የእሥራኤል ልጆች ፈጽመው በዝተዋል ፥ ከእኛ ም እነሱ ይጸናሉ ፥ ወደፊት ጠላት ቢነሣብን ከእነርሱ ወገን ተሰልፈው ይወጉናል ፥ አንድም ከበዙ ዘንድ አገራችንን ያስለቅቁናል። ብሎ ገና ለገና ፈርቶ ነው። ፈሪ ሰው ጨካኝ በመሆኑም፦ « ኑ ብልሃት እንሥራባቸው ፤ ጡብ እናስጥላቸው ፥ ኖራ እናስወቅ ጣቸው ፥ ጭቃ እናስረግጣቸው ፤ ይህን ሲያደርጉ ከዋሉ ልሙዳነ ፀብእ አይሆኑም ፥ አንድም ከድካም ብዛት ከሚስቶቻቸው አይደርሱም ፥ ካልደረሱም አይባዙም ፥ ካልበዙም አኛን አያጠፉም ፤ » አለ። ይኽንንም ብሎ አልቀረም። በብዙ ማስጨነቅ ፌቶም ፥ ራምሴንና ዖን የተባሉ ጽኑ ከተሞችን በግንብ አሠራቸው።
  
እስራኤል ዘሥጋ መከራ የሚያጸኑባቸውን ያህል እንደ መከራው ብዛት  እየበዙ ይጸኑ ነበር። ግብጻውያን ግን የእሥራኤልን ልጆች ያስመርሯቸው ፥ እየገፉ እያዳፉ በግፍዕ ይገዟቸው ነበር፡፡ በሕይወት መኖርን በሚያሰቅቅ ሥራ ሰውነታቸውን ያስጨንቋት ነበር። ከዚህም ሌላ ንጉሥ ዓቀብተ መወልዳትን ( አዋላጆችን ) ሾሞባቸዋል፡፡ እነርሱንም « ዕብራውያትን ሴቶች ስታዋልዱ ለመውለድ እንደደረሱ በአያችሁ ጊዜ ፥ ወንድ ቢሆን ግደሉት ፤ ሴት ብትሆን ግን አትግደሏት ፤ » አላቸው። እነርሱ ግን እግዚአ ብሔርን ፈርተው እንዳዘዛቸው አላደረጉም። ንጉሡም ጠርጥሮ አንድም ከነገረ ሰሪ ሰምቶ ፦ « ለምን ያዘዝኳችሁን አልፈጸ ማችሁም ? » ብሎ ጠየቃቸው፡፡ ምክንያቱም ወንድ ልጅ ተወልዶ ከሦስት ወር በኋላ ሲያለቅስ ፥ ሲያነጥስ በድምጹ ይታወቃልና ነው።  ሴቶች ምክንያት አያጡምና ( ብልሆች ናቸውና )፦ « የዕብራ ውያን ሴቶች እንደ ግብፃውያን ሴቶች አይደሉም ፥ አዋላጅቱ ሳትመጣ ወልደው ይቆያሉ ፤ » ብለው መለሱለት። እነርሱ ለእስራኤል በጐ ነገር በማድረጋቸው ፥ እግዚአብሔር ለእነርሱም በጐ አደረገላቸው ፤ ንጉሡ እንዳይገድላቸው አደረገ። ( የንጉሥ ትእዛዝ መተላለፍ ያስገድላልና )። ከፍ ብሎ በእግዚአብሔር ቸርነት ፥ ዝቅ ብሎ በአዋላጆች ደግነት እሥራኤል እጅግ በዝተው በረቱ። ያንጊዜም ፈርዖን ተቆጥቶ « ከዕብራውያን የሚወለደውን ወንድ ወንዱን ከፈሳሽ ውኃ ጣሏቸው ፥ ሴት ሴቱን ግን በሕይወት ተዉአቸው ፤ » የሚል አዋጅ አናገረባቸው።
  
 
          የእንባ ሰው ራሔል የነበረችው በዚህ ዘመን ነው። ሮቤልም ስምዖንም የሚባል ባል ሞቶባት ሐዘንተኛ ነበረች። እርሱ ሲሞት ነፍሰ ጡር ብትሆንም « በእርሱ ምትክ ኖራ ውቀጪ ፥ ጭቃ ርገጪ፤ » ተባለች። መንታ ፀንሳ ኑሮ ደም ፈሰሳት ሕፃናቱም ወጥተው ፥ ወጥተው ፥ ከጭቃው ወደቁ ። ደንግጣ ብትቆም ፥ ምን ያስደነግጥሻል ? የሰው ደም ፥ የሰው ሥጋ ጭቃውን ያጸናዋል እንጂ ምን ይለዋል ብለሽ ነው? ርገጪው ፤ » አሏት ፡፡ በዚህን ጊዜ ነው ፥ « ኢሀሎኑ በዝ ሰማይ አምላከ እሥራኤል ፤ በውኑ በዚህ ሰማይ የእስራኤል አምላክ የለምን ?» ብላ እንባዋን ያፈሰሰችው። ይኽንንም እንባ በእፍኟ እየሰፈረች ወደ ላይ ረጨችው። «እንደገናም ጌታ እግዚአብሔር ከፊት ሁሉ እንባን ያብሳል፤» እንዲል ፤ ኢሳ ፳፭ ፥ ፰ ፤ እንባን የሚያብስ እግዚአብሔር በሰማይ እንዳለ ታምናለችና። እንባዋ ወደ ምድር አልተመለሰም ፥ ከመንበረ ጸባዖት ደረሰ እንጂ ። « ወዐበየት ተናዝዞ ወነጊፈ ላህ ፤ ልቅሶ መተውን መጽናናትን እንቢ አለች።» ምክንያቱም ግፉ ያሳዝናልና ፥ የሕፃናቱ ሞት የፃር ነውና ፥ ሐዘን በየደጁ ኹኗልና፡፡ « እስመ ኢኮንዋ ውሉዳ ውሉደ ፤ ልጆቿ ልጆች አልሆኗትምና ፥» ሙተዋልና ፥ ባሌ ቢሞት በልጆቼ እጽናናለሁ። ያለችው ከንቱ ኹኖባታልና ። « ወኢሀለዉ በሕይወተ ሥጋ የለምና ፤» መጽናናትን እንቢ አለች፡፡ ይኽንን ነው ፥ ነቢዩ ኤርምያስ « የኀዘን የልቅሶና የጩኸት ድምፅ በራማ ተሰማ ፤ ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች ፤ » ያለው።
          የራሔል እንባ እግዚአብሔር እንዲናገር ፥ በረድኤትም እንዲወርድ አድርጐታል። « ሰማዕኩ ገዓሮሙ ለሕዝብየ ፥ ወወረድኩ ከመ አድኅኖሙ ፤ የሕዝቤን ጩኸት ሰማሁ ፥ ላድናቸውም ወረድኩ ፤» አሰኝቶታል። « እግዚአብሔርም ሙሴን በግብፅ ያሉ የወገኖቼን መከራ አይቼ ፥ በሠራተኞች የተሾሙ ሹማምንት ካመጡባቸው መከራ የተነሣ ጩኸታቸውን ሰምቼ ፥ መጨነቃቸውን አውቄላቸዋለሁ። ከግብጻውያን እጅ አድናቸው ፥ ወደ ተወደደችም ሰፊ ወደምትሆን ወደ ከነዓንም እወስዳቸው ዘንድ ወረድኩ። ከግብፅም አውጥቼ ማርና ወተት ወደሚጐርፍባት ፥ ተድላ ደስታ ወደማይታጣባት አገር እወስዳቸዋለሁ ፤ » አለ። ማር ያለው ሕገ ኦሪትን ነው ፥ ማር የነካው ጨርቅ በውኃ ቢያጥቡት ፈጥኖ እንዲለቅ ሕገ ኦሪትም የሚለቅ ሕግ ነበርና። ወተት ያለው ደግሞ ሕገ ወንጌልን ነው። ወተት (ቅቤ) የነካው ጨርቅ በውኃ ቢያጥቡት እንደማይለቅ ሕገ ወንጌልም የማትለቅ ( ጸንታ የምትኖር ) ሕግ ናትና ። ዘጸ ፫ ፥ ፰ ፡፡
          በአዲስ ኪዳን ደግሞ ከላይ እንደጠቆምነው ፦ ጌታ በተወለደ ጊዜ የአይሁድ ንጉሥ የነበረ ሄሮድስን በግብር ፈርዖንን መስሎ እናገኘዋለን ፡፡ የሩቆቹ ወርቅ ዕጣንና ከርቤ ይዘው ፥ በኮከብ እየተመሩ ሁለት ዓመት ተጉዘው ሲመጡ የቅርቡ ሄሮድስ ግን ዜና ልደቱ አስደነገጠው ። ጥያቄያቸው ፦ « አይቴ ሀሎ ንጉሥ ዘተወልደ ፤ የተወለደው ንጉሥ ወዴት ነው ? » የሚል ነበርና ። ዓለም የሥልጣን ነገር ያሳስበዋል ፥ የደነገጠ አውሬም ያደርገዋል ። የደነገጠ አውሬ ማንንም እንደማይምር ዓለምም እንዲሁ ነው።
          ሄሮድስ ኮከቡ የታየበትን ዘመን ከሰብአ ሰገል በጥንቃቄ ከተረዳ በኋላ በልቡ ፦ «ለካ ያ ብላቴና ሁለት ዓመት ሆኖታል ፤» አለ። ካህናቱን በስውር ጠርቶ በተረዳውም መሠረት « ቤተልሔም ነው፤ » ብሎ ሰደዳቸው። ከዚህም ጋር ፦ « ሄዳችሁ የብላቴናውን  ነገር ጠይቃችሁ እርሱን ያገኛችሁት እንደሆነ እኔም እንድሰግድለት በእኔ በኲል ተመልሳችሁ ንገሩኝ፤ » አላቸው፡፡ እርሱ በሽንገላ ቢናገረውም ነገሩ ጥበበ እግዚአብሔር ነው። ሰብአ ሰገል፦ « ለካስ የሀገሩም ነገሥታት ያምኑበታልሳ ፤ » በሚል ሃይማኖታቸው እንዲጸናላቸው ነው ።
          ሰብአ ሰገል ግን ሳጥኖቻቸውን ከፍተው ወርቅ እጣን ከርቤ ለሕፃኑ ከገበሩለት በኋላ መልአኩ እንደነገራቸው በሌላ ጐዳና ፥ በሌላ ኃይለ ቃል ፥ በሌላ ሃይማኖት ተመልሰዋል ። በሌላ ጐዳና ሁለት ዓመት የተጓዙትን በአርባ ቀን ገብተዋል፡፡ በሌላ ኃይለ ቃል « ወዴት ነው?» እያሉ መጥተው ነበር ፥ « አገኘነው ፤ » እያሉ ተመልሰዋል፡፡ በሌላ ሃይማኖት « ምድራዊ ንጉሥ ፤» እያሉ መጥተው ነበር ፥ ሰማያዊ ንጉሥ ፥ የባሕርይ አምላክ » እያሉ ተመልሰዋል።
          ሄሮድስ ሰብአ ሰገል እንደዘበቱበት  ( ባንተ በኩል እንመለሳለን ብለው በሌላ ጐዳና እንደሄዱ ) በሰማ ጊዜ ፈጽሞ ተበሳጨ። ጭፍራዎቹን ልኮ ከሰበአ ሰገል እንደተረዳው ዘመን ልክ ሁለት ዓመት የሆናቸውን ፥ ከዚያም የሚያንሱትን  ፥ በቤተልሔምና በአውራጃዎችዋ ሁሉ የነበሩትን አሥራ አራት እልፍ ሕፃናት አስገደለ። ያን ጊዜ ፦ በነቢዩ በኤርምያስ ፦ « ራሔል ስለ ልጆችዋ ስታለቅስ ብዙ ልቅሶና ዋይታ ተሰማ ፤ መጽናናትንም እንቢ አለች ፤ ልጆቿ የሉምና። » የተባለው ተፈጸመ ፥ ይላል። ራሔልን አነሣ እንጂ ልያን አላነሣትም። ምክንያቱም ጌታ የተወለደው ከልያ ወገን ስለተወለደ ዕዳዋ ነው። ራሔል ግን ከእርሷ ወገን ስላልተወለደ ያለ ዕዳዋ ነው። አንድም የልያ በርኅቀተ ሀገር በብዛት ድነውላታል ፤ የራሔል ግን በማነስ በቅርበት አልቀውባታልና ነው። አንድም በራሔል የልያንም መናገር ነው። አንድም « እናታችን ራሔል ኑራልን ፥ መከራችንን አይታልን ባለቀሰችልን ፣» ብለው ስላለቀሱ ነው። አንድም እንድናለን መስሏቸው ከመቃብረ ራሔል ገብተዋል ፥ ከዚያም ተከትለው ገብተው ልጆቻቸውን ከእቅፋቸዋ ነጥቀው ፥ አንገታቸውን ጠምዘው አርደውባቸዋል። በዚህን ጊዜ አፅመ ራሔል አንብቷል።  የራሔል መቃብር ከቤተልሔም አንድ ኪ.ሜ. ይርቃል።
          በሌላ በኲል ደግሞ ከልያም ከራሔልም ወገን የተወለዱትን ሊያገናኝ የሚችለውን አባታቸውን ያዕቆብን አላነሣም። ያነሣው እናታቸውን ራሔልን ነው። ምክንያቱም፦ ወንድ ልጅ ለአቅም አዳም ፥ ሴት ልጅ ለአቅመ ሔዋን ደርሰው የሞቱ እንደሆነ ኀዘን በአባት ይጸናል። በሕፃንነት ዘመን የሞቱ እንደሆነ ግን ኀዘን በእናት ይጸናልና ለዚህ ነው ።
          ቅዱስ ማቴዎስ « ራሔል » ብሎ ትንቢተ ኤርምያስን የጠቀሰው ለዚህች ብቻ ሳይሆን በግብፅ ለነበረችውም ነው። ይኸውም ግፍን ከግፍ ሲያነፃፅር ነው።
እነዚህን ሁሉ ሕፃናት እንዴት አድርጎ ሰበሰባቸው?
          ሄሮድስ አሥራ አራት እልፍ ሕፃናት የሰበሰበው « ንጉሡ ቄሣር ፦  ሕፃናትን ሰብስበህ ፥ ልብስ ምግብ እየሰጠህ ፥ በማር በወተት አሳድገህ ፥ ለወላጆቻቸው ርስት ጉልት እየሰጠህ ጭፍራ ሥራልኝ ብሎኛል፤ » የሚል አዋጅ አናግሮ በጥበብ ነው። ያላቸው ልጆቻቸውን፥ የሌላቸው ደግሞ ልብስ ምግብ ልቀበልበት ብለው እየተዋሱ ሄደዋል። እንዲህ አድርጎ ሰብስቦ ፈጅቷቸዋል። ለሁለቱም የግፍ ታሪኮች «የኀዘን የልቅሶና የጩኸት ድምፅ በራማ ተሰማ፤» የተባለው በመላእክት ዘንድ ተሰማ ፥ ማለት ነው። ምክንያቱም ኢዮር ፥ ራማ ፥ ኤረር ዓለመ መላእክት ናቸውና። አንድም በመላእክት ፈጣሪ በእግዚአብሔር ዘንድ ተሰማ ማለት ነው። ምክንያቱም መላእክት ባሉበት እግዚአብሔር አለ። አንድም ራማ የተባለች መንግሥተ ሰማያት ናት። ምሥጢራዊ ትርጉሙም ሃይማኖት ይዞ ምግባር ሠርቶ የሚገባባት አጥታ ታዝናለች ፥ ታለቅሳለች ማለት ነው።
          በዚህ ዘመን የሚያስፈልገው ሌላ ነገር ሳይሆን ይህ የራሔል እንባ ነው። ዓለም በግፍ ተከድናለችና ፥ ነፃ ሰው የለምና። «ረከሱ በበደላቸውም ጐሰቈሉ ፥ በጎ ነገርን የሚያደርጋት የለም። እግዚአብሔርን የሚፈልግ አስተዋይ እንዳለ ያይ ዘንድ እግዚአብሔር ከሰማይ የሰው ልጆችን ተመለከተ ሁሉ ተካክሎ በአንድነት በደለ ፤ አንድ ስንኳ በጎ ነገርን የሚያደርጋት የለም፡፡ ሕዝቤን እንጀራን እንደ መብላት የሚበሉ ግፍ አድራጊዎች ሁሉ አያውቁም ፥ እግዚአብሔርን አይጠሩትም።» እንዲል፡፡ መዝ ፶፪ ፥ ፩-፬ ። ስለዚህ ፦
ሀ. ለራሳችን እናልቅስ ፤
          በሕገ እግዚአብሔር ጸንተን ባለመቆማችን ( ከፍቅረ እግዚአብሔርም ከፍቅረ ቢጽም በመለየታችን ) ልናለቅስ ይገባል። «ሕግህን አልጠበቅሁምና የውኃ ፈሳሾች ከዓይኖቼ ፈሰሰ ይላልና። መዝ ፩፻፲፰ ፥ ፩፻፴፭ ፤። ቅዱስ ዳዊት ብዙ ጊዜ ለራሱና ለቤተሰቡ አልቅሷል። በኦርዮና በቤርሳቤህ ምክንያት ነቢዩ ናታን በገሠጸው ጊዜ ፦ « እግዚአብሔርን በድያለሁ ፤ » ብል አለቀሰ። ነቢዩ ናታንም፦ እግዚአብሔር ደግሞ ኃጢአትህን አርቆልሃል ፥ አትሞትም። ነገር ግን በዚህ ነገር ለእግዚአብሔር ጠላቶች መነሣሣት ምክንያት አድርገሃልና ስለዚህ ደግሞ የተወሰደልህ ልጅ ፈጽሞ ይሞታል፤ » አለው። ዳግመኛም ቅጣቱ እንዲነሣለት ማቅ ለብሶ አመድ ላይ ተኛ ፥ ጾመ ፥ ለመነ ፥ ጸለየ ፥ አለቀሰ፡፡  እርሱም ራሱ « ሕፃኑ ሕያው ሳለ ፥ ምናልባት እግዚአብሔር ይምረኝ ፥ ሕፃኑም በሕይወት ይኖር እንደሆና ማን ያውቃል ብዬ ጾምሁ ፥ አለቀስሁም፤ » ብሎአል። ፪ኛ ሳሙ ፲፪፥፩-፳፫። ልጁ አቤሴሎም ባሳደደውም ጊዜ ተከናንቦ እያለቀሰ የደብረ ዘይትን አቀበት ወጥቷል፡፡ ፪ኛ ሳሙ ፲፭ ፥ ፴ ።
          ቅዱስ ዳዊት ወደ ውስጥ እየተመለከቱ ስለ ራስ በማልቀስ ያምን ነበር። ብዙ ጊዜም ውጤት አግኝቶበታል። ይኽንንም በመዝሙሩ ላይ ብዙ ቦታ ጠቅሶታል። « በጭንቀቴ ደክሜአለሁ ፥ ( ወድጄ በሰራሁት ሥራ ጠፋሁ ) ፥ ሌሊቱን ሁሉ አልጋዬን አጥባለሁ ፥ በዕንባዬም መኝታዬን አርሳለሁ። ዐይኔ ከቁጣ የተነሣ ታወከች ፥ ከጠላቶቼ ሁሉ የተነሣ አረጀሁ። ( ሰብአ ትካትን ፥ ሰብአ ሰዶም ፥ ሰብአ ገሞራን ባጠፋህበት መዓትህ ታጠፋኝ ይሆን ? ከማለቴ የተነሣ ዓይኔ ባከነች። ሴትና ልጅ አለንጋ ያነሡባቸው እንደሆነ ከአሁን አሁን ያሳርፉብን  ይሆን ብለው ዓይናቸው እንደሚባክን እኔ ባከንኩኝ። ከፍርድህ የተነሣ ሰውነቴ ባለ መከራ ሆነች። ከቁጡ ዕንባ የተነሣ ፊቴ ተንጣጣ ፥ ቅንድቤ ተመለጠ )። ከጠላቶቼ ሁሉ የተነሣ አረጀሁ። ( መከራ ስላጸኑብኝ ያለ ዕድሜዬ አረጀሁ ፥ እያልሁ እንደሌለ ሰው ሆንኩኝ ፥ ሳልሞት እንደ ሞተ ሰው ተቆጠርኩኝ )፡፡ ዓመፃን የምታደርጉ ሁሉ ፥ ከእኔ ራቁ ፤ ( ጐልማሳ ገደለ ፥ የጐልማሰ ሚሰት ነሣ ፥ እያላችሁ ከፈጣሪዬ ጋር የምታጣሉኝ ሰዎች አንድም አጋንንት ከእኔ ራቁልኝ ) ፤ እግዚአብሔር የልመናዬን ቃል ሰምቶአልና። ብሏል። መዝ ፮ ፥ ፮-፰። በሌላ ምዕራፍም፦ « ልቅሶዬን መልስህ ደስ አሰኘኸኝ። ማቄን ቀድደህ ደስታን አስታጠቅኸኝ። » ብሏል፡፡ መዝ ፳፱ ፥ ፲፩።
          ቅዱስ ዳዊት የችግሩ መፍቻ ቁልፍ ምንግዜም ቢሆን እውነተኛ እንባው ነበር። ጠላቶች ሲሰድቡት ፥ ጐረቤቶቹ ሲርቁት ፥ ዘመዶቹ ሲክዱት ፥ ያዩት ሁሉ ከእርሱ ሲሸሹ ፥ ሁሉም እንደሞተ ሰው ከልብ ሲረሳው ፥ እንደጠፋ ዕቃ ሲሆን ፥ በዙሪያው የከበቡትን ሰዎች የትዕቢት ድምፅ ሲሰማ ፥ ለክፉ ነገር ተባብረው ነፍሱን ለመንጠቅ ሲማከሩ እርሱ ግን በእግዚአብሔር ታምኖ እንፋሎት ያለው እንደ ፈላ ውኃ የሚያቃጥል እንባ በጉንጮቹ ላይ ያፈስ ነበር። መዝ ፴ ፥ ፱-፲፬። ጠላቶቹ ባመጡበት መከራ ደስ ሲላቸው ልቅሶው እናት እንደሞተችበት ሰው ነበር። መዝ ፴፬፥፲፱ ።
          ቅዱስ ዳዊት ስለ ራሱ የሚያለቅሰው « ለምን ይህ መከራ መጣብኝ ፤ » በማለት ሳይሆን በተአምኖ ኃጣውዕ (ኃጢአትን በመታመን) መከራውን እንዲያርቅለት ነው። መዝ ፴፯ ፥ ፲፰። ንጉሡ እዝቅያስም፦ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ  « ትሞታለህ እንጂ በሕይወት አትኖርምና ቤትህን አስተካክል ፤ » ባለው ጊዜ ፥ ወደ ግድግዳ ዞሮ እጅግ ታላቅ ልቅሶን በማልቀሱ ከበሽታው ተፈውሷል ፥ በዕድሜው ላይ አሥራ አምስት ዓመት ተጨምሮለታል። ሕዝ ፴፰ ፥ ፩-፭።
          ቅዱስ ጴጥሮስ ፦ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እርሱ የተናገረው ትንቢት በተፈጸመበት ጊዜ ወደ ወጭ ወጥቶ መራራ ልቅሶን አልቅሷል።
           ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የፈሪሳዊውን ግብዣ ተቀብሎ ከደቀመዛሙርቱ ጋር በማዕድ በተቀመጠ ጊዜ ፥ በዚያ አገር ካሉ ሰዎች ይልቅ ኃጢአተኛ የነበረች ሴት ሽቱ ይዛ መጣች። እያለቀሰች በዕንባዋ እግሩን አራሰችው ፥ በጠግሯም አበሰችው። እግሩን ትስመው ሽቱም ትቀባው ነበር። እንዲህም በማድረጓ ከሰባት አጋንንት ቁራኝነት አላቀቃት ፥ « እምነ ትሽ አድኖሻልና በሰላም ሂጂ፤ » አላት። ለእኛ የሚያስፈልገን እንዲህ ዓይነት ዕንባ ነው። ቅዱስ ጳውሎስ፦ « አሁን ለንስሐ ስላዘናቸሁ ደስ ብሎኛል እንጂ ስላዘናችሁ አይደለም። » ያለው ለዚህ ነውና። ፪ኛ ቆሮ ፯ ፥ ፱።
                                               ለ. ለትዳራችን እናልቅስ ፤
          ባል በሚስቱ ፥ ሚስትም በባሏ ግፍ እየፈጸሙ ነውና። « መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር ነው ፥ ለመኝታቸውም ርኵሰት የለውም ፤ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል። » የሚለው እንኳን ግብሩ ጥቅሱ ከጠፋብን ሰንብተናል። የሠርግ ሰሞን የጥሪ ወረቀታችንን እና ግድግዳችንን ያጨናነቀው እርሱ ነበር። ዳሩ ግን በወረቀት ላይ እንጂ በልባችን ላይ ስላልተጻፈ ፈጽሞ ተረስቷል። ዕብ ፲፫ ፥፬። ነገሩ ሁሉ፦ « ሚስት ታጫለህ ፥ ሌላም ሰው ከእርስዋ ጋር ይተኛል ፤ ቤት ትሠራለህ ፥ አትቀመጥበትም ፤ ወይን ትተክላለህ ፥ ከእርሱም አትበላም፤ » ሆኗል። ዘዳ ፳፰ ፥፴። ወንዶቹንም ቢሆን፦ « ሚስትህ ባልንጀራህን የቃል ኪዳንህ ሚስት ሆና ሳለች እርሷን አታልለሃታልና፤ » እያለን ነው ፥ እግዚአብሔር። ሚል ፪ ፥፲፬። ነገር ግን የሚያደምጥ ጠፍቶ ምድር ፍቺ በፍቺ ሆናለች። በአንድ ቤት ውስጥ እየኖርን በምንም ነገር የማንስማማ ፥ ላለመስማማት ተስማምተን ፥ ተናንቀን ፥ እጅ እጅ የሚል (የተሰለቸ) ኑሮ የምንኖር እንደተፋታን ነው  የምንቆጠረው። « ስለዚህ መንፈሳችሁን ጠብቁ ፥ ማንም የልጅነት ሚስቱን አያታልል። መፋታትን እጠላለሁ ፥ ይላል የእሥራኤል አምላክ እግዚአብሔር ፤ ልብሱንም በግፍ ሥራ የሚከድነውን ሰው እጠላለሁ ፥ ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ፤ ስለዚህ እንዳታታልሉ መንፈሳችሁን ጠብቁ። » ሚል ፪ ፥፲፮።
ሐ. ለልጆቻችን እናልቅስ
          ከልጅነት እስከ እውቀት ከልጆቹ ጋር ደክሞ በልጆቹ የሚደሰት ጠፍቷል፡፡ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭው ዓለም መስመር የለቀቁ ፥ ሰው ሰውኛውን እንዳይመለሱ ሆነው የጠፉ ፥ እንዳይነሡ ሆነው የወደቁ ልጆች ብዙዎች ናቸው። ጌታ በወንጌል፦ « እና ንተ የኢየሩሳሌም ልጆች ሆይ ፥ ለራሳችሁና ለልጆቻችሁ አልቅሱ እንጂ ለእኔስ አታልቅሱልኝ። መካኖች ፥ ያልወለዱ ማኅፀኖችና ያላጠቡ ጡቶችም የተመሰገኑ ናቸው ፥ የሚሉበት ወራት ይመጣልና። » ያለው በገሀድ እየታየ ነው። ሉቃ ፳፫ ፥፳፰። ንጉሥ ዳዊትን ተከታይ አብጅቶ ከዙፋኑ ያሳደደው ፥ በጦርነትም የተፋለመው የገዛ ልጁ አቤሴሎም ነው። « ዳዊትም ተከናንቦ ያለ ጫማ እያለቀሰ ወደ ደብረ ዘይት ዐቀበት ወጣ ፤ ከእርሱም ጋር የነበሩት ሕዝብ ሁሉ ተከናንበው እያለቀሱ ወጡ። » ይላል ። ፪ኛ ሳሙ ፲፭ ፥፴። በሃይማኖትም በኵል፦ የሊቀ ካህናቱ የዒሊ ልጆች ቤተ መቅደሱን ደፍረው ያሰደፍሩ ነበር። በዚህ የተነሣ አባታችው በእግዚአብሔር ቃል ተገሥጿል ፥ በመጨረሻም ከወንበር ወድቆ አንገቱ ተቆልምሞ ክፉ ሞት ሞቷል። ልጆቹም በጦር ሜዳ ተቀሥፈዋል። ፩ኛ ሳሙ ፪ ፥፳፪ -፳፮ ፣ ፬፥፲፪-፳፪ ።
መ. ለወገኖቻችን እናልቅስ፤
          አንድ ሕዝብ ፥ አንድ ወገን ስንሆን በዘር ተለያየተን እርስ በርስ እየተቋሰልን ነው። ከዚህ ንጹሕ የሆነ ሰው ማግኘት እጅግ ያስቸግራል። ዘረኝነትን በቃልም በጽሑፍም ፊት ለፊት የምናወግዘውም ቢሆን ከጀርባችን አዝለነው እንገኛለን። በዓለማውያን ዘንድ ብቻ አይደለም ፥ መንፈሳውያን በምንባለውም ጭምር ነው። አማርኛ ተናገሪው ሌላውን እንዳላይ እንዳልሰማ ይላል ፥ በውስጥ ግን ጐንደሬ ፥ ጐጃሜ ፥ ወሎዬ ፥ ሸዌ እያለ የተከፋፈለ ነው። እንዲህ እያለ ክፍፍሉ እስከ ጐጥ ድረስ ይወርዳል። ትግርኛ ተናጋሪውም ለጊዜው አንድ ይመስላል እንጂ፦ አድዋ ፥ ሽሬ ፥ አክሱም ፥ተምቤን ፥ አዲግራት እያለ የተከፋፈለ ነው። ኦሮምኛ ተናጋሪውም የሸዋ ፥ የወለጋ ፥ የአርሲ ፥ የሐረር ፥ የባሌ ፥ የቦረና እያለ የተከፋፈለ ነው። ለአብነት እነዚህን ጠቀስን እንጂ በሁሉም ያው ነው። ለጊዜው የምንስማማው ከእኛ ዘር ውጪ የሆነውን ለማጥቃት እንጂ በውስጣችን እሳትና ጭድ ነን። ሄሮድስና ጲላጦስ በውስጥ አይስማሙም ነበር ፥ በውጭ ግን ክርስቶስን ለመስቀል ተስማሙ። ሊቃውንቱ ክርስቶስ ፍቅር ስለሆነ በመሐል ሆኖ አስማማቸው ይላሉ። የእነርሱ መስማማት ለእርሱ ጉዳት ቢሆንም አስማማቸው ። እኛም ተጐድተንም ቢሆን ሰዎች እንዲስማሙ እናድርግ። መስሎን ነው እንጂ እንኳን ዘር ከአንድ ማኅፀን መውጣትም አያስማማም። ቃየል አቤልን ገድሎታል ፤ ዘፍ ፭ ፥ ፰። ዔሳው ያዕቆብን ሊገድለው አሳዶታል ፤ ዘፍ ፳፯ ፥ ፵፮፡፡ አቤሜሌክ የእናቱን ወገኖች አስተባብሮ በእናት የማይገናኙትን ሰበዓ የአባቱን ልጆች ( ወንድሞቹን ) ነፍሰ ገዳዮችን በገንዘብ ደልሎ አሳርዷቸዋል። መሳ ፱፥፩-፮። ሁላችንም « ዳግመኛ የተወለዳችሁት ከሚጠፋ ዘር አይደለም ፤ በሕያውና በዘለዓለም በሚኖር በእግዚአብሔር ቃል ከማይጠፋ ዘር ነው እንጂ። » የሚለውን ዘንግተናል። ማስታወስም አንፈልግም ፥ ብናስታውስም ለመፈጸም አቅም አጥተናል። ፩ጴጥ ፩ ፥፳፫ ።
ሠ. ለሀገራችን እናልቅስ
          በእነ ቅዱስ ዳዊት፦ « ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች ፤ . . . በፊቱም ኢትዮጵያ ይሰግዳሉ ፤ . . . ለኢትዮጵያ ሰዎች ምግባቸውን ሰጠሃቸው፤ » የተባለላት ሀገራችን እንዴት ናት? መዝ ፷፯፥ ፴፩ ፣ ፸፩ ፥፱ ፣ ፸፫ ፥፲፬። አባቶቻችን ሀገረ እግዚአብሔር ያሰኟት ሀገራችን ምን እየመሰለች ነው? እነ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የበቀሉባት ፥ እነ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የመነኑባት ፥ ተሰዓቱ ቅዱሳን የተጠለሉባት ኢትዮጵያ ይዞታዋ እንዴት ነው? የሚለውን ለመመለስ መጻሕፍትን ማገላበጥ ሊቃውንትን መጠየቅ የሚያስፈልግ አይመስለኝም። ነገራችን ሁሉ « ክምሬ ያለሽ መስሎሻል ፥ ተበልተሽ አልቀሻል ፤ ሆኗል። » በረከት ርቆናል ፥ ረድኤት ተለይቶናል። ይህም በሚበዛው መናገር እንጂ ፈጽሞ የለም ማለት አይደለም። የሃይማኖት ለዋጮች በዝተዋል ፥ በውስጥም በአፍአም አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ጠንክረዋል ፥ አሕዛብ ተበረታተዋል። « ኢትዮጵያ የክርስቲያን ደሴት » የሚለውን ለማጥፋት በሙሉ ኃይላቸው እየተረባረቡ ነው። « አቤቱ አሕዛብ ወደ ርስትህ ገቡ ፥ የቅድስናህንም መቅደስ አረከሱ ፤ » የሚለውም እየተፈጸመ ነው። መዝ ፸፰ ፥፩ ።
          ስለዚህ አገራችንን የረሳን ሁሉ ቅዱስ ዳዊትን አብነት አድርገን « ብረሳሽ ቀኜ ትርሳኝ ፤ ባላስብሽ ፥ ምላሴ ከጉሮሮዬ ትጣበቅ ፤ ከደስታዬ ሁሉ በላይ አገሬን ባልወድድ ፤ » እንበል። መዝ ፩፻፴፮፥፭። እንደ ነህምያ በሀገር ፍቅር እንቃጠል። ነህምያ የአገሩን ጥፋት በሰማ ጊዜ አመድ ነስንሶ ከአመድ ላይ ተቀምጦ አለቀሰ ፥ ማቅ ለበሰ ፥ አያሌ ቀን አዘነ ፥ በሰማይም አምላክ ፊት ጾመ ፥ ጸለየ። ነህ ፩ ፥፬።
          ስለ ሀገር ማሰብ ማለት፦ ስለ ወንዙና ተራራው ፥ ስለ ዳር ድንበሩ ብቻ አይደለም። ከዚህ ሁሉ ጋር ኢትዮጵያን ኢትዮጵያ ያሰኛትን ታሪክ ፥ ሃይማኖት ፥ ሥርዓት ፥ ትውፊት ፥ ቅርስና ፥ ሕዝብ ማሰብ ማዘን ማልቀስ ያስፈልጋል ። ዋናው ነገር በሃይማኖት የሚፈስ እንባ ነው። ያን ጊዜ ጩኸታችን እስከ ራማ ድረስ ይሰማል።
ረ. ስለ ቤተ ክርስቲያናችን አንድነት እናልቅስ ፤
          የቤተ ክርስቲያን አንድነት የሚመጣው « በእኔ እበልጥ፤ » መንፈስ አይደለም። « ካልተመለሳችሁ ፥ እንደዚህም ሕፃን ካል ሆናችሁ ወደ መንግሥተ ሰማያት ከቶ አትገቡም እነደዚህም ሕፃን ራሱን ዝቅ ያደረገ በመንግሥተ ሰማያት የሚበልጥ ይህ ነው፤ » በሚለው መንገድ ብቻ ነው። ማቴ ፲፰ ፥፫። ወንጌልም ቤተ ክርስቲያንም መንግሥተ ሰማያት ይባላሉ ።ሮሜ ፲፩ ፥፲፯። የግል ጥቅማችን እንዲጠበቅልን ቅድመ ኹኔታ በማስቀመጥም አይደለም። መቀበሉ እንደ ቀኖት ቢሰማንም ፥ እንደ ሆምጣጤ ቢመረንም « እኔ ይቅርብኝ ፥ እኔ ልጐዳ ፤» በማለት ነው። ክርስቶስ ሰውና እግዚአብሔርን  ፥ ነፍስና ሥጋን  ፥ ሰውና መላእክትን  ፥ ሕዝብንና አሕዛብን አንድ ያደረገው፣ በመስቀል ላይ ቆስሎ ነው። ስለሆነም ክርስቶስ ለቆሰለላት ቤተ ክርስቲያን ትንሽ ትንሽ እንቁሰልላት። አባቶቻችን ቅዱሳን ብዙ ቆስለውላታል ። የእነርሱ ልጆች ነን ካልን አሠረ ፍኖታቸውን እንደተሰጠን ጸጋ መጠን እንከተል። ሁላችንም ራሳችንን እንመርምር። በሌላ ዓይን ያለውን ጉድፍ ሳይሆን በእኛ ውስጥ የተተከለውን ትልቅ ምሰሶ እንመልከት። የወጭቱን ላዩን ሳይሆን ውስጡን እናጥራ፥ያን ጊዜ ውጪውም ይጠራል። ማቴ ፯ ፥፩ ፣ ፳፫ ፥ ፳፭። የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር ከተፈታ የአገሪቱም ችግር ይፈታል። የትዳራችንም የልጆቻችንም ችግር ይፈታል። በመሆኑም አስቀድመን ስለ ቤተ ክርስቲያናችን እናልቅስ። 
የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን ።
Source: http://www.betedejene.org/2010/10/blog-post_23.html

No comments:

Post a Comment