13

.

"በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው::" የማቴዎስ ወንጌል 7: 4

"እናንተ የተጠማችሁ ሁሉ፥ ወደ ውኃ ኑ፥ ገንዘብም የሌላችሁኑና ግዙ ብሉም ኑ ያለ ገንዘብም ያለ ዋጋም የወይን ጠጅናወተት ግዙ።" ትንቢተ ኢሳይያስ 55 : 1

Tuesday, November 29, 2011

“ምሥጢረ ሥላሴ”




በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

“ምሥጢረ ሥላሴ”
o        ሥላሴ ማለት ሦስትነት ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አንድ ሲሆን ሦስት፣ ሦስት ሲሆን አንድ ነው። ሦስት ብቻ ተብሎ አይቆምም፣ እግዚአብሔር አንድም ሦስትም ነው።
o        ስለዚህ እግዚአብሔር የአንድነትና የሦስትነት ባለቤት ስለሆነ ሥላሴ ይባላል።
o        እግዚአብሔር አንድ ነው ስንል፤
§   በመለኮት (ዘዳ.6፤4 “እስራኤል ሆይ ስማ አምላካችን እግዚአብሔር አንድ እግዚአብሔር ነው፤ አንተም አምላክህን እግዚአብሔርን በፍፁም ልብህ፣ በፍፁም ነፍስህ፣ በፍፁምም ኃይልህ ውደድ”)
§   በባህርይ
§   በሕልውና (ዮሐ. 14፤10 “እኔና አብ አንድ ነን”)
§   በአገዛዝ
§   በሥልጣን (ኢሳ. 66፤1 “እግዚአብሔር እንዲህ ይላል ሰማይ ዙፋኔ ነው ምድርም የእግሬ መረገጫ ናት የምትሠሩልኝ ቤት ምን ዓይነት ነው? የማርፍበትስ ስፍራ ምንድር ነው? እነዚህን ሁሉ እጄ ሠርታለችና እነዚህ ሁሉ የእኔ ናቸው።”)
§   ይህን ዓለም በመፍጠርና በማሳለፍ (ዘፍ. 1፤1-26 “እግዚአብሔርም ሰማይና ምድርን ፈጠረ….” ፣ መዝ.101፤25 “አቤቱ አንተ ከጥንት ምድርን መሠረትኽ ሰማያትም የእጅህ ስራዎች ናቸው” ፣ )እና በመሳሰሉት እግዚአብሔር (ሥላሴ) አንድ ነው።
o        ሥላሴ ሦስት ናቸው ስንል፤ በስም፣ በአካል፣ በግብር ሦስት ናቸው ይህም፤
§ በስም ሦስትነት
·         ስም የሚለው ከራስ ጠጉር እስከ እግር ጥፍር ያለውን የአንድ ሰው አካል ከሌላው ሰው አካል ተለይቶ ማን እንደሆነ ታውቆ የሚጠራበት ነገር ነው።
v      ስም  “አብ፣ ወልድ፣ መንፈስቅዱስ” ነው። ሰው ሰው መባልን የሚያገኘው አካሉ ሲገኝ እንደሆነ ሁሉ እንደዚሁም አብ ወልድ መንፈስቅዱስ የሚባለው ስም ምንም እንኳን ሥላሴ በዚህ ጊዜ ተገኙ የሚባልበት ጊዜ ባይኖርም፣ ጥንት መሠረት ሳይኖረው ቅድመ ዓለም ሲኖር የኖረ ነው። (ማቴ.28፤19)
§       በአካል ሦስትነት
·         ከራስ ጠጉር እስከ እግር ጥፍር ድረስ ያለውን “አካል” የሚለው ቃለ ያመለከታል።
·         ገጽን፣ መልክእን አቋምን ያመለክታል ይህም ማለት፣
1.     ገጽ፡ ሲል ልብስ የማየሸፍነውን ከአንገት በላይ ያለውን መገለጫ መታወቂያን ግንባርን ያመለክታል። ስለዚህ የሰው መታወቂያው መገለጫው ከአንገቱ በላይ ያለ ፊቱና ግንባሩ ስለሆነ አንድ ሰው ፊቱን ቢሸፍን ወይም ከአንገቱ በላይ ያለው አካል ቢጠፋ (ቢቆረጥ) ቀሪው አካሉ ሁሉ ቢታይ ማን እንደሆነ ሊታወቅ አይቻልም።
2.     መልክእ፡ የምንለው ቀይ ጥቁር የሚለው ይከተለዋል። ግብርን መልካም ክፉ ማለት ሲከተለው ደግሞ ቅርጽን ደም ግባትን ያመለክታል። ይኸውም ቀይ መልክእ ጥቁር መልክእ፣ መልከ መልካም እንደማለት ነው።
v      ስለዚህም አብ ፍጹም መልክእ ፍጹም ገጽ ፍጹም አካል አለው፣ ወልድም ፍጹም መልክእ ፍጹም ገጽ ፍጹም አካል አለው፣ መንፈስቅዱስም ፍጹም መልክእ ፍጹም ገጽ ፍጹም አካል አለው።

§ በግብር ሦስትነት
ግብር፡ የሚለው ከግዕዝ ገብረ ከሚለው ግስ የተገኘ ሲሆን ሥራ፣ ተግባር ማለት ነው።
·         አብ ማለት አባት ማለት ነው።
·         ወልድ ማለት ልጅ ማለት ነው።
·         መንፈስቅዱስ ማለት ሠራጺ (የወጣ፣ የሚሰርጽ) ማለት ነው።
v      አብ ወላዲ እና አሥራፂ፣ ወልድ ተወላዲ፣ መንፈስቅዱስ ሠራጺ የሥላሴ የግብር ሦስትነት ነው።
·         አብ ወልድን ቢወልድ መንፈስቅዱስን ቢያሠርጽ እንጂ አይወለድም አይሰርጽም፣ ወልድም ቢወለድ እንጂ አይወልድም አይሰርጽም፣ መንፈስቅዱስም ቢሠርጽ እንጂ አይወልድም አይወለድም።
o       ሥላሴ በቅድምና እኩል ናቸው።
v      ሥላሴ በቅድምና አንድ ናቸው። በነፍስ ምሳሌነት ስንመለከት፡ ልብ ከቃል ከእስትንፋስ ጋር በአንድነት አንድ ጊዜ ይገኛል እንጂ ከቃል ከእስትንፋስ ቀድሞ መገኘት የለበትም ቃልም ከእስትንፋስ ከልብ ፤ እስትንፋስክ መልብ ከቃል ቀድሞ መገኘት የለባቸውም እንደዚህም
v      አብ ከወልድ ከመንፈስቅዱስ አይቀድምም ቀድሞ የተገኘበት ጊዜ የለም፣ ወልድም ከመንፈስቅዱስ አይቀድምም ቀድሞ የተገኘበት ጊዜ የለም ወልድም ከመንፈስቅዱስ አይቀድምም ቀድሞ የተገኘበት ጊዜ የለም መንፈስቅዱስ አይቀድምም መንፈስቅዱስ ከወልድ በዃላ አይሆንም።
o      የሥላሴ ምሳሌ
§         በመሰረቱ ምሳሌ ከሚመሰልለት ነገር እንደሚያንስ የታወቀ ነው። በመሆኑም ምሳሌ አድርገን ከስነ ፍጥረት የምናቀርባቸው ሁሉ ፍጹም የእግዚአብሔርን አንድነትና ሦስትነት ይገልጣሉ ለማለት ሳይሆን መጠነኛ ግንዛቤ ይሰጣሉ በማለት አበው ለምሥጢረ ሥላሴ ምሳሌ አድርገው ያቀረቧቸውን እንገልጻለን።
1.    ሥላሴ በነፍስ ይመሰላሉ
1.     ከሰው ነፍስ የበለጠ ለሥላሴ ምሳሌ የሚሆን አይገኝም ምክንያቱም እግዚአብሔር ራሱ ሰውን በመልኩና በአርአያው መፍጠሩን ገልጿልና ሰው እግዚአብሔርን የሚመስለው በነፍሱ ነው። (ዘፍ.1፤26) ነፍስ በአካልዋ አንድ ስትሆን በከዊን (በሁኔታ) ሦስት ናት። ይኸውም ልብ መሆን፣ ቃል መኾን እስትንፋስ መኾን ነው። ልብ፣ ቃል፣ እስትንፋስ የነፍስ ባህርያት ናቸው። ነፍስ በአካልዋ አንድ ስትሆን ሦስት ባህርያት አሏት። የነፍስ አካልዋ አንድ እንደሆነ ሁሉ ሥላሴም በመለኮት በባህርይ በህልውና አንድ ናቸው። አካልዋ አንድ የሆነ ነፍስ ሦስት ከዊን እንዳላት ሁሉ ሥላሴም በመለኮት አንድ ሲሆኑ በስም በአካል በግብር ሦስት ናቸው።
2.     ነፍስ በአካሏ ከሦስት የማትከፈል አንዲት ስትሆን በባህርይዋ እንደ ሥላሴ ሦስት ከዊን አላት። በባህርይዋ ያለ ሦስት ከዊን አካሏን ከሦስት እንደማይከፍለው ሁሉ በሥላሴ ባህርይ ያለ ሦስት ከዊንም ባህርየ ሥላሴን፤ መለኮተ ሥላሴን ከሦስት አይከፍለውም።
3.     በባህርይዋ ሦስት ከዊን (ሁኔታ) ያላት ነፍስ (ይህም ልባዊነት፣ ነባቢነት (ቃልነት)፣ ሕይወትነት) አንዲት ብትባል እንጂ ሦስት እንደማትባል ሁሉ ሦስት ከዊን ያላት መለኮተ ሥላሴ ባህርየ ሥላሴም አንዲት ብትባል እንጂ ሦስት አትባልም።
4.     በልብነቷ አብ፣ በቃልነቷ ወልድ፣ በእስትንፋስነቷ መንፈስቅዱስ ይመሰላል። ልብነቷ ቃልነትን እስትንፋስነትን ያስገኛል እንጂ ቃልነቷን ወይም እስትንፋስነቷ ልብነቷን አያስገኝም። ቃልነቷ እስትንፋስነትዋን እስትንፋስነትዋ ቃልነትዋን ሊያስገኝ አይችልም። እንዲህ ማለት ቃል እስትንፋስ ከልብ ይመነጫል እንጂ ልብ ከቃል ከእስትንፋስ አይገኝም፣  ቃልም እስትንፋስን እስትንፋስ ቃልን ሊያስገኝ አይችልም ማለት ነው። እንደዚሁም በቃል የተመሰለ ወልድ በእስትንፋስ የተመሰለ መንፈስቅዱስ በልብ የተመሰለ ከቸብ ይገኛሉ እንጂ አብ ከወልድ ከመንፈስቅዱስ አይገኝም። በቃል የተመሰለ ወልድም በእስትንፋስ የተመሰለ መንፈስቅዱስን አያስገኝም። በእስትንፋስ የተመሰለ መንፈስቅዱስም በቃል የተመሰለ ወልድን አያስገኝም። (ዮሐ. 15።26 “ዳሩ ግን እኔ ከአብ ዘንድ የምልክላችሁ አጽናኝ እርሱም ከአብ የሚወጣ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ፥ እርሱ ስለ እኔ ይመሰክራል፤…)

2.    ሥላሴ በፀሐይ ይመሰላሉ
1.     ለፀሐይ 3 አካል አለው ይህም ክበብ፣ ብርሃን ሙቀት ናቸው። በክበቡ አብ፣ በብርሃኑ ወልድ በሙቀቱ መንፈስቅዱስ ይመሰላሉ። ክበቡ ሙቀትን ብርሃንን ያስገኛል እንጂ ብርሃን ሙቀትን ክበብን አያስገኝም ሙቀትም ክበብን ብርሃንን አያስገኝም።እንደዚሁም በክበብ የተመሰለ አብ በብርሃን የተመሰለ ወልድን በሙቀት የተመሰለ መንፈስቅዱስን ያስገኛል እንጂ በብርሃን በሙቀት የተመሰሉ ወልድ መንፈስቅዱስ በክበቡ የተመሰለ አብን አያስገኙትም።
2.     ፀሐይ አንድ ስትሆን ሦስት ነገሮች ስላሏት ሦስት እንደማትባል ሁሉ ሥላሴም በመለኮት አንድ ሲሆኑ በአካላት ሦስት ናቸው፣ ዳሩ ግን በአካላት ሦስት ስለሆኑ ሦስት አምላክ አይባሉም አንድ አምላክ እንጂ አትናቴዎስ ሐዋርያ እንደተናገረ “አብ አምላክ ነው፣ ወልድም አምላክ ነው፣ መንፈስቅዱስም አምላክ ነው አንድ አምላክ እንላለን እንጂ ሦስት አማልእክት አንልም።”
3.     ብርሃን ሙቀትን ፣ሙቀት ብርሃንን ሊያስገኝ እንደማይችል መንፈስቅዱስ ወልድን ወልድም መንፈስቅዱስን ሊያስገኝ አይችልም።
4.     ክበብ ሲገኝ ብርሃን ሙቀት አብረው ይገኛሉ እንጂ ክበብ ቀድሞ ብርሃን ሙቀት ኋላ የሚገኙ አይደለም። እንደዚሁ ወልድ መንፈስቅዱስ እንደ አብ ቅድመ ዓለም ህልዋን ናቸው እንጂ አብ በዘመን ቀድሟቸው ኋላ የተገኘ አይደሉም።
5.     ክበበ ፀሐይ ብርሃንን ሙቀትን እየላከ መኖሩን ያስታውቃል እንጂ እንደ ብርሃን እንደ ሙቀት የሚላክ አይደለም። እንደዚሁ አብ ወልድን መንፈስቅዱስን እየላከ ህልውናውን ይገልጸል እንጂ ለማንም የታየና የተገለጸ አይደለም። (ዮሐ. 1፤ 18 “መቼም ቢሆን እግዚአብሔርን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ በአባቱ እቅፍ ያለ አንድ ልጁ እርሱ ተረከው።” እንዲል)ስለዚህም ቅዱሳት መጻሕፍት አብን ላኪ ወልድን እና መንፈስቅዱስን ተላኪ እያሉ ይነግሩናል እንጂ በሥላሴ መቀዳደም መከተል መቅደም የለባቸውም።


3.    ሥላሴ በእሳት ይመሰላሉ።
1.     እሳት ሦስትነት አለው፣ ነበልባል፣ ብርሃን፣ ዋዕይ (ሙቀት) ናቸው። በነበልባሉ አብ፣ በብርሃኑ ወልድ፣ በዋዕዩ (በሙቀቱ) መንፈስቅዱስ ይመሰላሉ። ነበልባል ብርሃንንና ሙቀትን ያስገኛል እንጂ ብርሃንና ዋዕይ ነበልባልን አያስገኙም። እንደዚሁ አብ ወልድንና መንፈስቅዱስን ያስገኛል እንጂ ወልድና መንፈስቅዱስ አብን አያስገኙም። እንደዚሁም ብርሃን ዋዕይ፣ ዋዕይ ብርሃንን ሊያስገኝ እንደማይችል፣ በብርሃን የተመሰለ ወልድ በዋዕይ የተመሰለመንፈስቅዱስን ሊያስገኝ አይችልም፣ መንፈስቅዱስም ወልድን ሊያስገኝ አይችልም።
2.     እሳት ሦስት ነገሮች ስላሉት እሳቶች አይባልም አንድ እሳት ይባላል እንጂ፣ ሥላሴም አንድ አምላክ ይባላል እንጂ 3 አማልእክት አይባልም፣ አይደለም።
3.     ነበልባል ከብርሃን ከዋዕይ መቅደም መብለጥ እንደሌለበት ለብርሃንና ለዋዕይም ከነበልባል ማነስ ወይም ወደኋላ መሆን እንደሌለባቸው አብም ከወልድ ከመንፈስቅዱስ አይቀድምም አይበልጥም። ወልድ መንፈስቅዱስም ከአብ አያንሱም በዘመን ወደኋላ አይሉም፣ ወልድም ከመንፈስቅዱስ አይበልጥም አያንስም መንፈስቅዱስም ከወልድ አያንስም አይበልጥም።
4.     ነበልባል ብርሃኑን ፈንጥቆ ጨለማን በማራቁ፣ ዋዕዩን ልኮ በማሞቁ ህልውናውን (መኖሩን) እንዲያሳውቅ፤ የአብም ህልውናው በወልድ በመንፈስቅዱስ ስለገለጸ ነው እንጂ በሥላሴ መቅደም መቀዳደም መብለጥ መበላለጥ ኖሮባቸው አይደለም።


ማጠቃለያ
እንግዲህ ከብዙው በጥቂቱ በመጽሐፍቅዱስ ውስጥ ስለ ሥላሴ የተጻፈውን ገልጸናል። ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ምንም እንኳን በጥራዝ ነጠቅነት የተነሱ አጽራረ ሥላሴ አማልእክተ ብዙ እያሉ ሊነቅፏት ቢከጃጅሉም እርሷ ግን እንደ አሕዛብ በብዙ አማልክት አታምንም።  “እስራኤል ሆይ ስማ አምላካችን እግዚአብሔር አንድ እግዚአብሔር ነው።” ዘዳ.6፤4 የሚለው አምላካዊ ትዕዛዝ መመሪያዋ ነው። ነገር ግን አንዱ መለኮት በስም በአካል በግብር ሦስት ነው ብላ ታምናለች። ይህም እምነትዋ በቅዱሰት መጻሕፍት የተደገፈ እንጂ ጠላቶችዋ እንደሚያወሩባት ከአሕዛብ የተወረሰ ባእድ አምልኮ አይደለም። ምሥጢረ ሥላሴ ከ5ቱ ዓዕማደ ምሥጢራት ውስጥ የመጀመሪያው ሲሆን የሃይማኖታችን መሠረት ነው። ምሥጢር ማለት ለልጅ፣ ለታማኝ ሰው ብቻ የሚነገር ሲሆን ይህም ምሥጢረ ሃይማኖትን ማወቅ የሚችለውና የሚነገረው እምነቱን በእግዚአብሔር ላይ ላደረገ፣ በ40ና በ80 ቀን ከመንፈስቅዱስ የተወለደ፣ እግዚአብሔርን በሃይማኖትና በምግባር ለማስደሰት የሚተጋ፣ የቤተክርስቲያን ልጅ ለሆነ ብቻ የሚነገርና የሚማሩት ትምህርት ነው። ስለዚህም ሁላችንም ረቂቅና ምጡቅ የሆነውን የሰው አዕምሮ ተመራምሮ ከማይደርስበት ከምሥጢረ ሥላሴ ትምህርት ውስጥ እጅግ በጣም ጥቂቱን በዚህ ትምህርታችን ተምረናልና የበለጠ በሰፊው ለመማር የሚቻለው ይህንን ትምህርት በቅድሚያ ተረድተው ሲያውቁና ሲያምኑ ስለሆነ በደንብ ማጥናትና ማወቅ ይገባል እንላለን።
እንግዲህ ቅዱስ መጽሐፍ እንደመሰከረው እግዚአብሔር የማይደመር ሦስት የማይከፈል አንድ ነው። በመለኮቱ አይከፈልም ሦስቱ አካላትም ተጠቅለው አንድ አይሆኑም።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር
ምንጭ፡ ፍኖተ ጽድቅ (በብርሃኑ ጎበና በ1986 ዓ.ም በአርቲስቲክ ማተሚያ ቤት የታተመ)
የቦሌ መንበረ ብርሃን ቅዱስ እግዚአብሔር አብ ቤተክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት
 

1 comment:

  1. To understand more about Trinity , be Abraham . so that God will appear to you with this secret.

    ReplyDelete