13

.

"በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው::" የማቴዎስ ወንጌል 7: 4

"እናንተ የተጠማችሁ ሁሉ፥ ወደ ውኃ ኑ፥ ገንዘብም የሌላችሁኑና ግዙ ብሉም ኑ ያለ ገንዘብም ያለ ዋጋም የወይን ጠጅናወተት ግዙ።" ትንቢተ ኢሳይያስ 55 : 1

Thursday, September 15, 2011

የቅዱስ ጳውሎስ ሐዋርያዊ ሥራ

የመጀመሪያው የቅዱስ ጳውሎስ ጉዞ

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከኢየሩሳሌም ወደ አንጾኪያ ከተመለሰ በኋላ በልዑል እግዚአብሔር ጥሪ (የሐዋ. 13.1-3) በአሕዛብ ሀገር ወንጌልን ለመስበክ ከበርናባስ ጋር ወጡ፡፡ በዚህ ጉዞቸው በጠቅላላ ወደ 2000 ኪ.ሜ የሚደርስ መንገድ በእግር ተጉዟል፡፡ ይህም ጉዞ የተከናወነው በ46 ዓ.ም አካባቢ ነው፡፡ የተሸፈኑትም ሀገሮች ሲሊንውቂያ፣ ቆጵሮስ፣ ስልማና፣ ጳፋ፣ ጰርጌን፣ ገላትያ፣ ጵስድያ፣ ኢቆንዮን፣ ሊቃኦንያ፣ ልስጥራ፣ ደርቤን፣ ጵንፍልያ፣ አታልያ እና አንጾኪያ ናቸው፡፡




ሁለተኛ የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ ጉዞ
ቅዱስ ጳውሎስ እና ማርቆስ 
ሁለተኛው ጉዞ የተከናወው በ50 ዓ.ም ገደማ ነው፡፡ በመጀመሪያው ጉዞ ማርቆስ አብሮ ተጉዞ ነበር፡፡ ነገር ግን ጵንፍልያ ከተማ ሲደርስ እናቱ ስለናፈቀችው መመለስ በመፈለጉ በርናባስ ወደ ኢየሩሳሌም ይዞት መጣ፡፡ ስለዚህም በሁለተኛው ጉዞው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲላስን ይዞ ወደ ኪልቋያ ሶርያ ሲጓዝ በርናባስ ደግሞ ማርቆስን አስከትሎ ወደ ቆጵሮስ ሄደ፡፡ በዚህ ጉዞው ቅዱስ ጳውሎስ እስከ ግሪክ ደርሶአል፡፡ የተጓዘባቸውና ያስተማረባቸው ከተሞችም፡- ደርብያ፣ ልስጥራ፣ ፍርግያ፣ ገላትያ፣ ሚስያ፣ ጢሮአዳ፣ ሳሞትራቄ፣ ናፒሊ፣ ፊልጵስዩስ፣ ተሰሎንቄ፣ በርያ፣ አቴና፣ ቆሮን፣ ቶስ፣ አንክራኦስ፣ ኤፌሶን፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌም እና አንጾኪያ ናቸው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመንፈስ ልጁ ጢሞቴዎስን ያገኘው በዚሁ ጉዞው በልስጥራ ከተማ ነው፡
 ሦስተኛው የቅዱስ ጳውሎስ ጉዞ
     ይህ ጉዞ የተከናወነው በ54 ዓ.ም ሲሆን የተሸፈኑትም ሀገሮች የሚከተሉት ናቸው፡፡
ገላትያ፣ ፍርግያ፣ ኤፌሶን፣ መቄዶንያ፣ ፊልጵስዩስ፣ ቆሮንቶስ፣ ጢሮአዳ፣ አሶን፣ ሚሊጢኒን፣ አንጠቀከስዩ፣ ትሮጊሊዩም፣ መስጡ፣ ቆስ፣ ሩድ፣ ጳጥራ፣ ጢሮስ፣ ጵቶልማይስ፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌም፡፡

ክርስቲያኖች የሰበሰበውን ዕርዳታ ለኢየሩሳሌም ቤተ ክርስቲያኖች በመያዝ ሦስተኛውን ጉዞ አጠናቅቆ ኢየሩሳሌም ገባ፡፡ ነገር ግን ኢየሩሳሌም የገባበት ጊዜ የፋሲካ በዓል ስለነበር ከልዩ ልዩ ሀገሮች የተሰበሰቡ አይሁድ በከተማዋ ነበሩ፡፡ እነዚህ በዝርወት የሚኖሩ አይሁድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን በየሀገራቸው በትምህርቱ የተነሣ ሲቃወሙት የነበሩ ናቸው፡፡

እኒህ አይሁድ ቅዱስ ጳውሎስን በኢየሩሳሌም ሲያዩት ታላቅ ተቃውሞ አነሡበት፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ተቃውሞአቸውን ለመግታት እንደ አይሁድ ሕግ በቤተ መቅደስ የመንጻት ሥርዓት መፈጸም ጀመረ፡፡ ነገር ግን ከኤፌሶን የተከተለውን ጥሮፊሞስን ወደ መቅደስ ያስገባው ስለመሰላቸው ተቃውሞአቸው በረታ፡፡ የሐዋ. 22.29፡፡ ከተማውንም አወኩት፤ ይህ ነበር ቅዱስ ጳውሎስን በ58 ዓ.ም ለሮም እሥር የዳረገው፡፡
 ከብዙ መከራና ስቃይ በኋላ ታሥሮ ሮም ገባ፡፡ በዚያም በቁም እሥር ሆኖ ለሁለት ዓመታት ያህል ወንጌል ሰበከ፡፡ የሁለቱን ዓመት የቁም እሥር እንደጨረሰ ወደ ኔሮን ፍርድ ቤት ቀረበ፡፡ ይህም በ60ዎቹ ዓ.ም ነው፡፡ በፍርድ ቤቱ በተደረገው ምርመራ የሮሜን ሕግ የሚቃወም ምንም ወንጀል ስላልተገኘበት በነፃ ተለቀቀ ::

የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ ጉዞዎች


አራተኛው የቅዱስ ጳውሎስ ጉዞ
ከዚህ በኋላ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አራተኛውንና የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ያልመዘገበውን ጉዞውን ያደረገው፡፡ ይህ ጉዞው በመታሠሩ አዝነው ተክዘው የነበሩ ክርስቲያኖችን ለማጽናናት የጀመራቸውን ሥራዎች ፍጻሜ ለማየት የተደረገ ጉዞ ነው፡፡ በዚህም ጉዞው ኢየሩሳሌምን፣ ኤፌሶንን፣ ሎዶቅያን፣ መቄዶንያን፣ ቀርጤስን፣ ጢሮአዳን፣ ድልማጥያን፣ እልዋሪቆን፣ ኒቆጵልዮን፣ ብረንዲስን፣ ጐብኝቷል፡፡ በዚህ የመጨረሻ የስብከት ጉዞው ለአራት ዓመታት ያህል ቆይቷል፡፡
ሰማዕትነት
በመጨረሻ በ64 ዓ.ም ኔሮን በጥጋቡ የሮማ ከተማ ስትቃጠል ምን እንደምትመስል ማየት እፈልጋለሁ ብሎ አቃጠላት፡፡ የሮም ሕዝብ በከተማው መቃጠል በማዘኑና በማመፁ ነገሩን ሁሉ በክርስቲያኖች ላይ አሳበበ፡፡ በዚህም የተነሣ ክርስቲያን የተባለ ሁሉ መሰደድ፣ መሠየፍ፣ መታረድ፣ ዕጣ ፈንታው ሆነ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም በኒቆጵልዮን ከተማ ሲያስተምር በ65 ዓ.ም ተይዞ ወደ ወኅኒ ገባ፡፡ ለሁለት ዓመት ከስድስት ወር በጨለማ ቤት ታሥሮ ከቆየ በኋላ በ74 ዓመት ዕድሜው በሮማ ከተማ በኦስትያ መንገድ አንገቱን ተሠይፎ በ67 ዓ.ም ሐምሌ አምስት ቀን በሰማዕትነት ዐረፈ፡፡

በአጠቃላይ 
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ :-


ዕውቀትን ከትህትና ደርቦ የያዘ ነበር፡- ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በኢየሩሳሌም በሚገኘው በታላቁ የአይሁድ ትምህርት ቤት በሊቁ በገማልያል እግር ሥር ብሉይ ኪዳንን የተማረ ነበር፡፡ በኋላም ትምህርተ ክርስትናን ከሐዋርያት አግኝቷል፡፡ ይህን ሁሉ ዕውቀት ይዞ ሁል ጊዜ ኑሮው የትህትና ነበር፡፡ እኔ ጭንጋፍ ነኝ እስከማለትም ደርሶ ነበር፡፡ (1ቆሮ. 15.8)

ትጉህና ታታሪ ነበረ፡- ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስለ42 ዓመታት ያህል በሐዋርያነት አገልግሎአል፡፡ እስከ እስጳኝ ድረስ ሄዶም አስተምሯል፡፡ በባሕር እና በእግር፣ ተመላልሷል፡፡ በ12ቱም ሐዋርያት ሀገረ ስብከት እየገባ ወንድሞቹን አግዞአቸዋል፡፡

ትዕሥተኛ ነበረ፡- ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ሰዎች በላከው ቀዳማዊ መልእክቱ እንደገለጠው (11.25-33) ብዙ ፈተናዎችን አልፏል፡፡ ሁለት ጊዜ ታሥሯል ተደብድቧል፣ በረሃብ ተገርፏል ይህ ሁሉ ቢሆንም በኑሮው ደስተኛ ነበር፡፡ በሮሜ ታሥሮ እያለ ለፊልጵስዩስ ሰዎች መልእክት ስጽፍ በደስታ የተሞላ ነበረ፡፡ በመጀመሪያ ጉዞው ያልተቀበሉትን ከተሞች በሁለተኛው አልያም በሦስተኛ ጉዞው ጎብኛቸው እንጂ እምቢ አሉኝ ብሎ ተስፋ አልቆረጠም፡፡

ጥበበኛ ነበረ፡- ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን የቤተ ክርስቲያን አበው (መዶሻ) ይሉታል፡፡ መዶሻ ማዕድናቱን ቀጥቅጦ አንደ ያደርጋቸዋል፤ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም በትምህርቱ ሕዝብንና አሕዛብን አንድ ያደረገ ሐዋርያ ነው፡፡ በ50 ዓ.ም አካባቢ ወደ ኢየሩሳሌም ሲወጣ ቲቶንና በርናባስን አስከትሎ ነበር፡፡ ቲቶን ከአሕዛብ ወገን በርናባስን ደግሞ ከአይሁድ፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ ሰውን እንዴት መቅረብ እንደሚቻል የሚያውቅ ሰው ነበረ፡- ከተራ ሰዎች እስከ ነገሥታት ቤተሰቦች በፍቅር እየሳበ ክርስቲያን አድርጓቸዋል፡፡ በመልእክቱ መጨረሻ የቤተክርስቲያን ልጆች በስማቸው እየጠራ ሰላምታ ማቅረብ የዘወትር ልማዱ ነበረ፡፡ ይህም ሁሉም በልቡ እንደታተሙ ያውቁ ዘንድ ነው፡፡

ጸሐፊ ነበር፡- ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በቃል ያለ ይረሳል በጽሑፍ ያለ ይወረሳል ነውና ያስተማራቸውን ክርስቲያኖች እንዲሁ አይተዋቸውም፡፡ ለሃይማኖታቸው ማጽኛ ለመንፈሳዊ ሕይወታቸው መመሪያ የሚሆኑ መልእክታትን ጽፎላቸዋል፡፡ አብዛኛዎቹ መልእክታት በእሥር ቤት ውስጥ ነው፡፡ ለመጓዝ የሚያስችለው አመቺ ጊዜ ሲያገኝ በአካል፣ በቃል፣ ያስተምራቸዋል፡፡ ሲታሠር መንቀሳቀስ ሲከለከል ደግሞ ጣቶቹ ብዕር ይጨብጣሉ፡፡ መልእክቶቹ በየሀገረ ስብከቱ ይላካሉ፡፡

ሥራ ወዳድ ነበር፡- ቅዱስ ጳውሎስ ሌት ተቀን ለስብከተ ወንጌል ቢባክንም ለምእመናን እንዳይከብድባቸው ድንኳን እየሰፋ የዕለት ጉርሱን የዓመት ልብሱን ያገኝ ነበር፡፡ የሐዋ. 18.3፣4 ለዚህም ነው ‹ሊሠራ የማይወድ ቢኖር አይብላ› እያለ ያስተምር የነበረው፡፡ 2ተሰ.3.10፡፡

የምሥራቅ ቤተክርስቲያን ሊቃውንት ከመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ ሲተላለፍ የኖረውን ትውፊት በማሰባሰብ ስለ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ተክለ ሰውነት እንዲህ ይላሉ፡፡
ጭንቅላቱ ትልቅ ሲሆን ራሰ በራ ነበር፡፡ የሁለቱም ቅንድቦቹ ጠጉር የተጋጠው፣ ዓይኖቹ ሰማያዊ ቀለም ያላቸው ሲሆኑ ዘወትር ብሩሃን ነበሩ፡፡ አፍንጫው ትልቅና ቀጥ ብሎ የወረደ ጽሕሙና ሪዙም ረጃጅም ናቸው፡፡ አንገቱ አጠር ያለ ሆኖ ትከሻው ክብና ጐባባ እግሮቹ ደግሞ ከጉልበቱ ላይ የተቃረቡ ናቸው፡፡ ቁመቱ አጠር ያለ ደንዳና ሰው (ከድንክ የረዘመ) እንደነበር ይነገርለታል፡፡


ዋቢ፡-
·        መጽሐፍ ቅዱስ
·        ዜና ሐዋርያት
·        ቤተክርስቲያንህን ዕወቅ
·         ትንሳኤ መጽሔት

ቅዱሳን ሐዋርያት ክፍል ፪

ዲያቆን መልአኩ እዘዘው የኔነህ
የሐዋርያት ዝርዝር
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሐዋርያት ዝርዝር በአራት ቦታዎች ተጽፎ ይገኛል፡፡ እነዚህ ዝርዝሮች በማቴዎስ፣ በማርቆስና በሉቃስ ወንጌሎች ሲገኙ በዮሐንስ ወንጌል ግን ዝርዝሩ አልሠፈረም፡፡ የመጨረሻው ዝርዝር የሚገኘው በሐዋርያት ሥራ ላይ ነው፡፡



ማቴዎስ 10.1-4
ማርቆስ 3.16-19
ሉቃስ 6.13-16
የሐዋ. ሥራ 1.13-14
ጴጥሮስ
ጴጥሮስ
ጴጥሮስ
ጴጥሮስ
እንድርያስ
ያዕቆብ ወ/ዘብዴዎስ
እንድርያስ
ዮሐንስ
ያዕቆብ ወ/ዘብዴዎስ
ዮሐንስ
ያዕቆብ ወ/ዘብዴዎስ
ያዕቆብ ወ/ዘብዴዎስ
ዮሐንስ
እንድርያስ
ዮሐንስ
እንድርያስ
ፊልጶስ
ፊልጶስ
ፊልጶስ
ፊልጶስ
በርተሎሜዎስ
በርተሎሜዎስ
በርተሎሜዎስ
ቶማስ
ቶማስ
ማቴዎስ
ማቴዎስ
በርተሎሜዎስ
ማቴዎስ
ቶማስ
ቶማስ
ማቴዎስ
ያዕቆብ ወ/እልፍ.
ያዕቆብ ወ/እልፍዮስ.
ያዕቆብ ወ/እልፍዮስ.
ያዕቆብ ወ/እልፍዮስ.
ታዴዎስ
ታዴዎስ
ስምዖን ቀነናዊው
ስምዖን ቀነናዊው
ስምዖን ቀነናዊው
ስምዖን ቀነናዊው
የያዕቆብ ይሁዳ
የያዕቆብ ይሁዳ
ያስቆሮቱ ይሁዳ
ያስቆሮቱ ይሁዳ
ያስቆሮቱ ይሁዳ
-



ይህ የሐዋርያት ዝርዝር በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ብቻ ሳይሆን በቤተ ክርስቲያን አዋልድ መጻሕፍትም በልዩ ልዩ ቦታ ይገኛል፡፡ ለምሳሌ ያህልም የገድለ ሐዋርያትንና የቅዳሴ ማርያምን መመልከት ይቻላል፡፡

ገድለ ሐዋርያት
ቅዳሴ ማርያም
ጴጥሮስ
ጴጥሮስ
እንድርያስ
ያዕቆብ
ያዕቆብ ወ/ዘብዴዎስ
ዮሐንስ
ዮሐንስ
እንድርያስ
ፊልጶስ
ፊልጶስ
በርተሎሜዎስ
በርተሎሜዎስ
ማቴዎስ
ቶማስ
ቶማስ
ማቴዎስ
ያዕቆብ ወ/እልፍዮስ.
ያዕቆብ ወ/እልፍዮስ.
ታዴዎስ
ታዴዎስ
ስምዖን ቀነናዊው
ስምዖን
ያስቆሮቱ ይሁዳ
ማትያስ

ከ12 ሐዋርያት መካከል ጴጥሮስ፣ ዮሐንስ ያዕቆብ፣ እንድርያስ፣ ቶማስ፣ ማቴዎስ፣ ስምዖን ቀነናዊ፣ ያዕቆብ ወልደ እልፍዮስ፣ በርተሎሜዎስና ፊልጶስ በአራቱ የመጽሐፍ ቅዱስ የሐዋርያት ዝርዝሮችና በሁለቱ አዋልድ መጻሕፍት ላይ ስማቸው ሳይለወጥ የሚገኝ ሲሆን ያስቆሮቱ ይሁዳ ደግሞ ታንቆ በመሞቱ የተነሣ በሐዋርያት ሥራ ላይ ስሙ ባይጠቀስም በሦስቱ ወንጌላውያን መጻሕፍትና በገድለ ሐዋርያት ላይ ተጽፎአል፡፡
ሐዋርያው ማትያስ የተተካው በዚሁ ሐዋርያ ምትክ ነው፡፡ በቅዳሴ ማርያም ላይም አባሕርያቆስ ስሙን ጠቅሶት ይገኛል፡፡
ታዴዎስ ከአራቱ የመጽሐፍ ቅዱስ የሐዋርያት ዝርዝሮች በሁለቱ እና በሁለቱ አዋልድ መጻሕፍት ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ የያዕቆብ ይሁዳ (ከአስቆሮቱ ይሁዳ ለመለየት) ደግሞ በቀሩት ሁለቱ ማለትም በሉቃስ ወንጌልና  በሐዋርያት ሥራ ላይ ተመዝግቦአል፡፡
ማቴዎስና ማርቆስ እንዲሁም ገድለ ሐዋርያትና ቅዳሴ ማርያም ታዴዎስ በሚለው ስሙ ሲጠሩት ወንጌላዊው ሉቃስ ግን በሁለቱም መጻሕፍቱ (በወንጌሉና በየሐዋርያት ሥራ) ‹የያዕቆብ ይሁዳ፣ የያዕቆብ ልጅ ይሁዳ›፣ በማለት ይጠቅሰዋል፡፡
በእሥራኤላውያን ዘንድ ከአንድ በላይ ስም የተለመደ ነው፡፡  ምክንያቱም ከብዙ ሕዝብ ጋር በመኖራቸውና የብዙ ቋንቋ ማለትም የግሪክ፣ የዕብራይስጥ፣ የአራማይክ፣ የሮማይስጥ ወዘተ. ተናጋሪዎች በመሆናቸው በልዩ ልዩ ቋንቋ ብዙ ስሞች አሏቸው፡፡
ለምሳሌ
·        ጴጥሮስ (ላቲን) ፤ ስምዖን (ዕብራይስጥ) ፤ ኬፋ (አራማይክ)
·        ቶማስ (ዕብራ) ፤ ዲዲሞስ (በግሪክ መንታ ማለት ነው፡፡)
·        ማቴዎስ - ሌዊ
·        ማርቆስ - (ሮማይስጥ)፣ ዮሐንስ (ዕብራ)
·        ሳውል (ዕብራ)፣ ጳውሎስ (ግሪክ)
በልዩ ልዩ ስም ተጠርተዋል፡፡ በዚህም መሠረት ታዴዎስም ‹ልብድዮስ-የያዕቆብ ይሁዳ› ተብሎ በሦስት ስም ተጠርቷል፡፡

የሐዋርያት ክብር በቤተ ክርስቲያን
ቅዱሳን ሐዋርያት የቤተ ክርስቲያን ቀዳማውያን አበው፣ ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተሠው፣ ሕይወታቸውን ለቤተ ክርስቲያን የሰጡ፣ በመሆናቸው በቤተ ክርስቲያን ዘንድ ልዩ ክብር አላቸው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም በልዩ ልዩ መንገድ ታከብራቸዋለች፡፡

ሀ. ትምህርታቸውን ሳታዛባ በመጠበቅ፡- በዙዎች በልዩ ልዩ ዘመን ከእውነተኛው ትምህርተ ሐዋርየት አፈንግጠዋል፡፡ በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን በሲሞን መሠርይ መሥራችነት ከተነሱት ግኖስቲኮች ጀምሮ በኋላ ዘመን እስከፈለቁት አርዮሳውያን፣ መቅዶንዮሳውያን፣ ሰባልዮሳውያን፣ ንስጥሮሳውያን፣ መሐመዳውያንና ሉተራውያን ድረስ ሐዋርያዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያቆየችላቸውን ትምህርተ ሐዋርያት፣ ትውፊት ሐዋርያትን ትተው በገዛ ፍልስፍናቸውና ምኞታቸው ፈቃድ ሲመሩ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግን የሐዋርያትን ትምህርትና ትውፊት ጠብቃ እስከዛሬ ኑራለች፡፡

ለ. ገድላቸውን በመመስከር፡- አበው ሐዋርያት የክርስትና ኑሮ ፋና ወጊዎች በመሆናቸው ከከሀድያን፣ ከመናፍቃን፣ ከአረማውያን፣ ከትዕቢተኛ መኳንንትና መሳፍንት፣ ከዚህ ዓለም የዲያብሎስ አሽከላ ጋር ተጋድለው በደማቸው ቀለም በአጥንታቸው ብዕር ነው - ክርስትናን የጻፉት፡፡ ጽፈውም ብቻ ሳይሆን ኑረው ቀምሰው አሳይተውናል፡፡ ‹እግዚአብሔር ቸር እንደሆነ  ቅመሱ እዩም› እንዳለ ልበ አምላክ ዳዊት
በሹክሹክታ የተማሩትን በጩኸት፣ በጨለማ የተማሩትን በብርሃን፣ በቤት የተማሩትን በሰገነት ገልጠውታል፡፡ በዚህ ጊዜም ጨለማ የሰፈነበት ዓለም የወንጌልን ብርሃን መቀበል ተስኖት ፍዳ መከራ አብዝቶባቸዋል፡፡ ይህ ያደረጉት ተጋድሎ ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ በገድላቸው፣ ወዘተ ይገኛል፡፡ ጽፎ መረከብ ማስተማርም ብቻ ሳይሆን በእግራቸው የተተኩ አበውም መንገዳቸውን ተከትለውታል፡፡
ዛሬም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሐዋርያትን ተጋድሎ ለትውልድ ሁሉ ትመሰክረዋለች፡፡ ልጆቿ አሠረ ፍኖታቸውን እንዲከተሉ ታስተምራቸዋለች፡፡ ልጆቿም ‹የሚበልጠውን ትንሣኤ እንዲያገኙ እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፡፡  ሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በእሥራትና በወኅኒ ተፈተኑ፡፡ በመጋዝ ተሠነጠቁ፡፡ በሠይፍ ተገድለው ሞቱ፡፡ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፡፡ ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፣ በዋሻና በምድር ጉድጓድ ተቅበዘበዙ፡፡› እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ ዕብራ. 11.38፡፡
ስለ ወንጌል ክብር፣ ስለ ርትዕት ሃይማኖት የተሠው፣ የቤተ ክርስቲያን መዓዛ የሆኑ ሐዋርያትን ገድል በተግባር ያውሉታል፡፡

ሐ. በዓላቸውን በማክበር፡- ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የቅዱሳን ሐዋርያት የሰማዕትነታቸውን (ከቅዱስ ዮሐንስ በቀር፣ እርሱ ግን ሳይሞት ወደ ብሔረሕያዋን ስለተወሰደ የተወለደበት ይከበራል፡፡ ዮሐ. 21.22፡፡) በዓል ታከብራለች፡፡ የጻድቅ ሞቱ በእግዚአብሔር ዘንድ የተከበረ ነውና፡፡
ይህ የሐዋርያት በዓል ከመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች ጀምሮ ይከበር ነበር፡፡ የሰርምኔሱ ሊቀ ጳጳስ ፖሊካርፐስ ሐዋርያት በሰማዕትነት ያረፉበት በዓል በጥንታውያን ክርስቲያኖች ዘንድ ይከበር እንደነበር በ2ኛው መ/ክ/ዘመን ላይ ዘግቦ ነበር፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የሐዋርያት በዓል በድምቀት በቤተ ክርስቲያን ይከበራል፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን የበዓላት ቀኖና መሠረት የቅዱሳን ሐዋርያት በዓል የሚከበርበት ዕለት እንደሚከተለው ነው፡፡
1. ዮሐንስ ወንጌላዊ                                         መስከረም 4 (ልደቱ)
2. ሐዋርያው ማቴዎስ                                    ጥቅምት 12
3. ሐዋርያው ፊልጶስ                                      ኅዳር 18
4. ሐዋርያው እንድርያው                              ታኅሳስ 4
5. ሐዋርያው ያዕቆብ ወ/እልፍዮስ                የካቲት 10
6. ሐዋርያው ማትያስ                                      መጋቢት 8
7. ሐዋርያው ያዕቆብ ወ/ዘብዴዎስ               ሚያዝያ 17
8. ሐዋርያው በርተሎሜዎስ                           መስከረም 1
9. ሐዋርያው ስምዖንን ቀነናዊ/ናትናኤል    ግንቦት 15
10. ሐዋርያው ቶማስ                                         ግንቦት 26
11. ሐዋርያው ታዴዎስ                                    ሐምሌ 2
12. ሐዋርያው ጴጥሮስ                                     ሐምሌ 5
13. ሐዋርያው ጳውሎስ                                    ሐምሌ 5

መ. በስማቸው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን በመሰየም:-አስቀድሞ እግዚአብሔር በነቢዩ በኢሳይያስ ቃል ‹ሰንበቴን ስለሚጠብቁ፣ ደስ የሚያሰኘኝንም ነገር ስለሚመርጡ፣ ቃል ኪዳኔንም ስለሚይዙ ጃንደረቦች እንዲህ ይላል፡- በቤቴና በቅጥር ውስጥ ከወንዶችና ከሴቶች ልጆች ይልቅ የሚበልጥ መታሰቢያና ስም እሰጣቸዋለሁ› ኢሳ. 56.4 ብሎ ለቅዱሳን ልጆቹ በገባው ቃል ኪዳን መሠረት ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ታቦት ተቀርፆላቸው በስማቸው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ተሠርቶላቸው ይከበራሉ፡፡

ሠ. በማቸው በመጠራት፡-  ቅዱሳን ሐዋርያት የቤተ ክርስቲያን መሠረት የክርስትና ፈር ቀዳጅ ናቸውና ዘወትር ሊታሰቡ ይገባል፡፡ በመሆኑም በክርስቲያኖች ዘንድ ክርስትና ከተነሱበት ዕለት ጀምሮ በስማቸው መጠራት ባህላችን ነው፡፡

ረ. ሥዕላቸውን በማክበር ፡- ከጥንቱ የካታኮምብ (ግበበምድር) ቤተ ክርስቲያን ጀምሮ የቅዱሳን ሐዋርያት ሥዕል ለሥርዓተ አምልኮ (ለጸሎት፣ ለምልጃና ለምሥጋና) መጠቀም የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ነው፡፡ ከዚያም በኋላ እስከ ዛሬ ድረስ የሐዋርያት ሥዕል በየአጥቢያ ቤተ ክርስቲያኑ ይገኛል፡፡ ምእመናንም አስቀድመው የልብሳቸውን ዘርፍ እየነኩ በጥላቸው ላይ እየተኙ ይፈወሱ እንደነበሩት ሁሉ የሐዋ. 5.15፣ 19.11 ዛሬም ሥዕላቸውን እየዳሰሱ ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስ ያገኙበታል፡፡


ሰ. በአማላጅነታቸው በመታመን ፡- የቅዱሳን አማላጅነት  በቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርትና በቤተ ክርስቲያን ታሪክ በተለያዩ ቦታዎች ተገልጦ ይገኛል፡፡ በዚህም መሠረት የቅዱሳን ሐዋርያት አማላጅነትም ከመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች ጀምሮ የታወቀ የታመነም ነው፡፡ በሮማ መንግሥት ጨካኝነት የተነሣ በግበበምድር ለመኖር የተገደዱት ጥንታውያን ክርስቲያኖች፣ በግበበ ምድሩ ግድግዳ ላይ በጻፉት ጸሎታቸው፤
‹ጳውሎስና ጴጥሮስ ሆይ ድል እናገኝ ዘንድ ጸልዩልን› ብለው የተናገሩት ተገኝቷል
                                                                                                                    ይቆየን
ዋቢ ፡ ቤተክርስቲያንህን ዕወቅ መጽሐፍ
        ዜና ሐዋርያት
Source: http://www.melakuezezew.info/2011/06/blog-post_24.html

ቅዱሳን ሐዋርያት ክፍል ፩

ዲያቆን መልአኩ እዘዘው የኔነህ
መግቢያ
መድኃኒተ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ በ30 ዘመኑ በማየ ዮርዳኖስ በዕደ ዮሐንስ ተጠምቆ 40 ቀንና ሌሊት በገዳመ ቆሮንቶስ ከጾመ ከጸለየ በኋላ የማስተማር ሥራውን ሲጀምር አስቀድሞ ያደረገው ነገር ቢኖር ቃሉን ተምረው ሰምተው ተአምራቱን አይተው ዳስሰው በዓለም ዞረው ወንጌልን የሚሰብኩ ደቀ መዛሙርቱን መምረጥ ነበር፡፡ እነዚህ ደቀ መዛሙርቱም ሐዋርያት ተብለው ይጠራሉ፡፡



ሐዋርያ የሚለው ቃል ሖረ-ሄደ ካለው የግእዝ ቃል የወጣ ሲሆን ትርጉሙም የተላከ ሂያጅ፣ ልዑክ ማለት ነው፡፡ ወንጌለ መንግሥትን ድኅነተ ዓለምን ለመላው ዓለም ሊያውጁ ሊያበሥሩ ተልከዋልና፡፡ ቅዱስ ማርቆስ በወንጌሉ እንደገለጠው (ማር. 3.13) አስቀድሞ ከእርሱ ጋር እንዲኖሩ ከጠራቸው በኋላ እግዚአብሔር ለሰው ልጅ የገለጠውን ድንቅ ሥራ አምላክ ሰው ሆኖ ያደረገውን ተአምራት ለዓለም ድኅነት የተደረገውን ሁሉ ሊመሠክሩ ተመርጠዋል፡፡
ከዚያ በፊት በሌዋውያን ዘር ይወርድ የነበረውን የብሉይ ኪዳን ሥልጣነ ክህነት በሐዲስ በመተካት ለእነርሱ ሰጣቸው ዮሐ. 20.22፡፡ እነርሱም ጌታችን እንዳስተማራቸውና ቃል ኪዳንም እንደገባላቸው፡፡ ማቴ. 28.20፡፡ ለተከታዮቻቸው ይኸንን ሥልጣን በአንብሮተ ዕድና በንፍሐት በመሾም አስተላለፉ፡፡ የሐዋ. 9.12፡፡በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተዋጀችውን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን በስብከታቸው በሰጣቸውም ሥልጣን ባደላቸውም ጸጋ ጠብቀው አቆዩዋት፡፡

የመጀመሪያዋ ቤተ ክርስቲያን በበዓለ ሃምሳ በቅዱስ ጴጥሮስ ስብከት በ3000 ምእመናን በሀገረ ኢየሩሳሌም በ0034 ዓ.ም ተመሠረተች፡፡ ከዚያም ዓለምን ዕጣ በዕጣ ተካፍለው ተዘዋውረው አስተማሩ፡፡ ወንጌልን ሰብከው ቤተ ክርስቲያንን አነፁ፡፡ አምልኮ ጣዖትን አጠፉ፡፡ ርኩሳን አጋንንትን አሳደዱ፡፡ በመስቀል ዕርፍ አርሰው ንጹሕ ዘር ወንጌልን ዘርተው በደማቸው አተሙ፡፡

ላስተማሩት  ሕዝብ ለእምነቱ ማጽኛ የሚሆኑ መልእክታትን ጻፉ፡፡ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ሠሩ፡፡ ከጌታ የተማሩትን ያዩትን እና የሰሙትን ለተከታዮቻቸው በቃልም በኑሮም በመጻሕፍትም አውርሰው በተጋድሎ ዐረፉ፡፡

የሐዋርያት አመራረጥ
ጌታችን ሐዋርያትን ከድኾችም ከሀብታሞችም መርጦአል፡፡ እነ ቅዱስ ጴጥሮስን የመሰሉ ድኻ ዓሣ አጥማጆችን ሲጠራ እነቅዱስ ማቴዎስን የመሰሉ በቀረጥ ብር የከበሩትንም አልተዋቸውም፡፡ ሁሉም በእግዚአብሔር ዘንድ እኩል ናቸውና፡፡ ሁሉም ደግሞ ያላቸውን ትተው ተከታትለውታል፡፡ ማቴ. 4.20፤ 9.9፡፡
         ከተማሩትም ከማይማኑም ወገን መርጦአል፡፡ ዮሐንስና ያዕቆብን ጌታ የጠራቸው ከአባታቸው ጋር ዓሣ ሲያጠምዱ ነው፡፡ ሌላ ትምህርት አልነበራቸውም፡፡ ነገር ግን አልናቃቸውም፡፡ ምሁረ ኦሪት የነበረውንም ናትናኤልን ጠርቶታል አልተወውም፡፡
የቀናተኞች አይሁድ ወገን በመሆኑ በዚያን ዘመን ሮማውያንን ለማስወጣት ውስጥ ውስጡን በምድረ ፍልስጥኤም ይካሄድ የነበረው ዐመፅ ተካፋይ የነበረውን ስምዖንን ከዚያ ግርግር አውጥቶ የሰላምና የፀጥታ ወደብ ወደ ሆነው ወደ እርሱ ወስዶታል፡፡
   ቤተ እሥራኤል ስትመሠረት 12ቱ አበው እየተባሉ በሚጠሩት ከያዕቆብ አብራክ በተከፈሉ የአሥራ ሁለቱ ነገድ አባቶች ነበር፡፡ አሁንም የእሥራኤል ዘነፍስ ማኅበር ቤተ ክርስቲያን ስትመሠረት በ12ቱ ሐዋርያት ትሆን ዘንድ አምላክ ፈቀደ፡፡
  1. ቅዱስ ጴጥሮስ - ከቤተ ስምዖን (በእናቱ ወገን) እናቱ ትወደው ስለነበር በነገድዋ ስም ጠራችው፡፡
  2. ቅዱስ እንድርያስ - ከቤተ ሮቤል (በአባቱ ወገን) አባቱ ይወደው ነበርና ከነገዱ በተወረሰ ስም ጠራችው፡፡
  3. ቅዱስ ያዕቆብ - ከነገደ ሌዊ (በአባቱ)
  4. ቅዱስ ዮሐንስ -  ከነገደ ይሁዳ (በእናቱ)
  5. ቅዱስ ፊልጶስ -  ከነገደ ዛብሎን
  6. ቅዱስ በርተሎሜዎስ - ከነገደ ንፍታሌም
  7. ቅዱስ ማቴዎስ - ከነገደ ይሳኰር
  8. ቅዱስ ቶማስ - ከነገደ አሴር
  9. ቅዱስ ያዕቆብ ወልደ እልፍዮስ - ከነገደ ጋድ
  10. ቅዱስ ታዴዎስ -  ከነገደ ዮሴፍ
  11. ቅዱስ ስምዖን ቀነናዊ - ከቤተ ብንያም
  12. ያስቆሮቱ ይሁዳ - ከቤተ ዳን


የሐዋርያት ሲኖዶስ
ሲኖዶስ ቃሉ የግሪክ ሲሆን ትርጉሙም ስለ ነገራተ ቤተ ክርስቲያን የሚሰበሰቡ  የቤተ ክርስቲያን አባቶች  ጉባዔ ማለት ነው፡፡

የመጀመሪያዋ የሐዋርያት ሲኖዶስ የተደረገችው በ50 ዓ.ም አካባቢ በኢየሩሳሌም ከተማ ሲሆን ለጉባዔው መደረግ ምክንያት የሆነውም በአንጾኪያ ቤተ ክርስቲያን ከይሁዲነት በተመለሱትና ከአረማዊነት በተመለሱት መካከል የተነሣውን ክርክር ለመፍታት ነበር፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት በተሰበሰቡ ጊዜ ሁሉ ስለ ነገረ ቤተ ክርስቲያን፣ ስለ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን፣ ስለ ካህናት አገልግለት ስለ ምእመናን ድርሻ፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ውሣኔዎችን አስቀምጠዋል፡፡ እነዚህ ‹እነርሱና መንፈስ ቅዱስ› በአንድ ላይ ሆነው የወሰኑዋቸው ውሣኔያት በሲኖዶስ፣ በአብጥሊስ፣ በግፅው፣ በዲደስቅልያ ወዘተ. መጻሕፍቶቻቸውና በቤተ ክርስቲያን ትውፊት ለኛ ደርሰውናል፡፡

ዛሬም በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዓመት ሁለት ጊዜ የሊቃነ ጳጳሳት ጉባዔ (ሲኖዶስ) የሚደረገው በዚሁ መሠረት ነው፡፡

አዕማድ ሐዋርያት
ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ለገላትያ ክርስቲያኖት በላከው መልእክቱ (2፡9) ጴጥሮስ፣ ዮሐንስ እና ያዕቆብን ‹አዕማድ ሐዋርያት› በማለት ጠርቷቸዋል፡፡ ይህ ስም ሊሰጣቸው የቻለበት ዐቢይ ምክንያት የኢየሩሳሌምን ቤተ ክርስቲያን በዋናነት ያስተባበሩ ስለነበር ነው፡፡
ከዚህም በተጨማሪ እነዚህ ሦስቱ ሐዋርያት ‹የምሥጢር ሐዋርያት› እየተባሉም ይጠራሉ፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ
·        በደብረ ታቦር ምሥጢረ መለኮቱን ሲገልጥ
·        በኢያኢሮስ ቤት ልጁን ሲፈውስ
·        በጌቴሴማኒ ሲጸልይ ከሌሎች ለይቶ ይዟቸው ሄዶ ነበር፡፡

ለሐዋርያት የተሰጠ ፀጋ
ጌታችን በቂሣርያ ከተማ ለሐዋርያት ያቀረበውን ጥያቄ በመመለሱ ቅዱስ ጴጥሮስን ‹የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ በሰማያት ያለው አባቴ እንጂ ሥጋ እና ደም ይህን አልገለጠልህም፡፡ አንተ ብፁዕ ነህ፡፡ እኔም እልኻለሁ አንተ ጴጥሮስ (ዐለት-በላቲን) ነህ፡፡ በዚህች ዐለትም ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሠራለሁ፡፡ የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም፡፡ የመንግሥተ ሰማያትን መክፈቻዎች እሰጥኻለሁ፡፡ በምድር የምታሥረው በሰማያት የታሠረ ይሆናል፡፡ በምድር የምትፈታው በሰማያት የተፈታ ይሆናል፡፡› ማቴ. 16.17-19 የሚለውን ቃል ተናግሮታል፡፡
ቅዱስ ጴጥሮስ ይህንን ለመባል የበቃው የክርስትና እምነት መሠረት የሆነውን ምሥጢረ ሥጋዌን - ምሥጢረተዋሕዶን በመመስከሩ ነው፡፡ አይሁድ የዮሴፍ ልጅ ነው፤ ሌሎቹ ደግሞ ከነቢያት አንዱ ነው፡፡ ሲሉ የክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት ቁልጭ አድርጎ በመመስከሩ ምስክርነቱም የእምነት መሠረት ነውና ‹ዐለት› ተባለ፡፡ የክርስትና እምነት መነሻው የእግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ሊያድነን ሊዋጀንም መጣ ብሎ ማመን ነው፡፡
ጌታችን ቅዱስ ጴጥሮስ ‹ዐለትነህ› ያለው ስለ እምነቱ ነው፡፡ ሰዎችን ታናሽ ወይም ታላቅ፣ ብፁዕ ወይንም ሌላ የሚያደርጋቸው እምነታቸው ነውና ለዚህ ነው ጌታችን በመዋዕለ ትምህርቱ ብዙ ጊዜ ‹እምነትህ(ሽ) ታላቅ ነው› ይል የነበረው፡፡
‹የመንግሥተ ሰማያት ቁልፍ› ለሐዋርያት የተሰጠውን ሥልጣነ ክህነት የሚያሳይ ነው፡፡
በምድር ያሠሩት፡- ከምእመናን ልቡና እያወጡ ያሠሩት ጠላት ዲያብሎስ፣ ርትዕት የሆነችውን ሃይማኖት ሊያጣምም ሲሞክር በስንዴው አዝመራ እንክርዳድን ሲዘራ ተገኝቶ አውግዘው የለዩት መናፍቅ በሰማያትም የታሠረ፣ የተለየ፣ የተወገዘ ይሆናል፡፡ እንኳንስ በሐዲስ ኪዳን ጥንት በሕገ ልቡና ዘመን አብርሃም የባረከውን ይስሐቅ፣ ይስሐቅ የባረከውን ያዕቆብ እግዚአብሔርም በሰማያት በረከት ሲባርካቸው የለዩዋቸውን እስማኤልንና ዔሳውን ደግሞ ከበረከቱ ለይቷቸዋል፡፡
በምድር፡- የፈታኸው፡- ዓለም በበደል በኃጢአት የታሠረ ነውና የኃጢአትን ገመድ በወንጌል ሰይፋቸው በጣጥሰው በፊት ቢፈቱለት በንስሐ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ከበደል እሥራት ቢፈቱት በሰማያት ፍርድ፣ በሰማያት መዝገብ የተፈታ ነፃም የወጣ ይሆናል፡፡
ይህ ሥልጣነ ክህነት ለቅዱስ ጴጥሮስ ብቻ የተሰጠ ሳይሆን ሐዋርያትን ሁሉ ወክሎ የተቀበለው ነው፡፡ ይህ ባይሆን ኖሮ በወንጌል ብርሃን የኃጢአትን ጨለማ እንዲገልጡ፣ የታሠሩትን እንዲፈቱ ጌታችን ሐዋርያትን ሁሉ ወደ ዓለም ባልላከም ነበር፡፡ መላክ የሚገባው ቅዱስ ጴጥሮስ ብቻ ነበርና፡፡
ይህንንም ሲያረጋግጥልን ጌታችን ለሐዋርያት የመንፈስ ቅዱስን ሀብት ባደለበት ሥልጣነ ክህነትን (አስቀድሞ የነገራቸውን፤  ያበሠራቸውን፣ ቃል ኪዳንም የገበላቸውን) ሲሰጣቸው ‹እፍ አለባቸውና መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ፡፡ ኃጢአታቸውንም ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል፡፡ የያዛችሁባቸውም ተይዞባቸዋል፡፡› በማለት ቀድሞ በቁልፍ የተመሠለ ሥልጣናቸውን አብራርቶ ተረጉሞ ነግሮዋቸዋል፡፡ ዮሐ. 20.22-23፡፡
ይህም ሥልጣን በአንብሮተ ዕድ ለቤተ ክርስቲያን ካህናት ተላልፎአል ይተላለፋልም፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንኳን ከተጠመቀ በኋላ ይህንን ሀብት በአንብሮተ ዕድ አግኝቶታል፡፡ የሐዋ. 9.12፡፡ እርሱም በፈንታው እነ ቅዱስ ጢሞቴዎስንና ቲቶን በዚሁ ሥልጣን ሾሟቸዋል፡፡ የመንፈስ ቅዱስ ልጁን ጢሞቴዎስንም ‹በማንም ላይ ፈጥነህ እጅህን አትጫን› በማለት ያዘዘው ይህንን ሥልጣነ ክህነት ለእግዚአብሔር ቤት አገልግሎት ለተመረጡ፣ ራሳቸውንም ወደው ፈቅደው ለለዩ፣ ለምእመናን አባት፣ መሪ መሆን ለሚችሉ ብቻ መስጠት ስላለበት ነው፡፡
ከሁሉም በላይ ደግሞ መድኃኒተ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ በሚያርግበት ሰዓት ‹እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ከእናንተ ጋር ነኝ› ማቴ. 28.20 በማለት የተናገረው ሐዋርያት ሳይሞቱ በዚህች ምድር የሚኖሩ ሆነው ሳይሆን በእነርሱ እግር ተተክተው ቤተ ክርስቲያንን ለሚያገለግሉ ካህናት ጭምር ይህንን የሐዋርያት ሥልጣን ማደሉን ሲናገር ነው፡፡ 
የሐዋርያት ትምህርት - ለቤተ ክርስቲያን
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተሰበከችው በሐዋርያት በመሆኑ ትምህርተ ሐዋርያት ከክርስቶስ የተገኘ የቤተ ክርስቲያን እምነት መነሻ ነው፡፡ የሐዋርያት ትምህርት በዓይን ያዩት፣ በጆሮ የሰሙት፣ በእጅ የዳሰሱት በኋላም በመንፈስ ቅዱስ የተረዱት ነውና እውነተኛነቱ የተረጋገጠ ነው፡፡
በመድኃኒተ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ‹ሂዱና አስተምሩ› ተብለው የታዘዙ ናቸውና መልእክተኛነታቸው የታመነ ነው፡፡ የእነዚህን ሐዋርያት ትምህርት ቤተ ክርስቲያን 1.ኛ በትውፊት 2.ኛ በመጻሕፍት አግኝታዋለች፡፡
1. ትውፊት
ሐዋርያት ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ ‹ከእኔ የተማራችሁትንና የተቀበላችሁትን፣ የሰማችሁትንም ያያችሁንትም እነዚህን አድርጉ› ፊልጵ 4.9 ፡፡ በማለት እንደተናገረው ሐዋርያት ያስተማሩት በመጻሕፍት ብቻ ሳይሆን ከኑሮአቸው፣ ከተግባራቸው፣ ከገድላቸው እና ከትሩፋታቸው ጭምር በመሆኑ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሐዋርየት  ትውፊት ትጠቀምበታለች፡፡
2. በሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት
የሐዋርያትን እውነተኛ ትምህርት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጠብቃ በመያዝ ለዓለም  አበርክታዋለች፡፡ ሐዋርያት ወንጌልንና መልእክታትን የጻፉት ያስረከቡትም ለቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ የሚገኘውም በቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ ባለቤትም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡
ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የትምህርቷ፣ የሥርዓቷና የሕጓ መሠረት መጽሐፍ ቅዱስ የሆነውም በዚሁ መሠረት ነው፡፡ 
                                                                     
ዋቢ ፡ ቤተክርስቲያንህን ዕወቅ መጽሐፍ
         ዜና ሐዋርያት

Source: http://www.melakuezezew.info/2011/06/blog-post_22.html